የጠቅላይ ቤተ ክህነት ጽ/ቤት: ዓመታዊውን ሀገር አቀፍ ሐዋርያዊ ሥምሪት ያካሒዳል

e18ba8e18ca0e18980e18888e18ba8-e18cb8e189a0e189b0-e18d80e188a8-e189b0e18890e18bb0e188b0-e18b90e189a0e18ba8-e18c88e189a0e18aa0

  • ሥልጠና፣ ውይይት፣ የቢሮና የመስክ ግምገማ፣ የሥምሪቱ ፕሮግራሞች ናቸው
  • ከዕቅበተ እምነት ጀምሮ የ45 አህጉረ ስብከት እንቅስቃሴዎች ይገመገሙበታል
  • ከሰበካ ካህናትና የሰንበት ት/ቤት ተወካዮች እስከ ሥ/አስኪያጆች ይሳተፉበታል
  • ከጠቅ/ጽ/ቤትና ከቅ/ሲኖዶስ የሚጠበቁ የድጋፍና ክትትል አግባቦች ይለዩበታል

†††

  • ማኑዋሎችና የልኡካኑ አቅም፣“ቤት ያፈራው” ቢኾንም፣ሊታሰብበት ይገባል
  • በሰበካ ጉባኤ ምሥረታ ዓመታት፣ የአደራጅ አባቶችን ተጋድሎ ያስታውሰናል
  • አሳታፊ እና ግልጽ ውይይት እንዲኖር አድርጉ፤/ብፁዕ ዋናሥራ አስኪያጁ/
  • “ጠቅላይ ሚኒስትሩ ያሉትንም ይዛችኹ አስተምሩበት፤”/ቅዱስ ፓትርያርኩ/

†††

የመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተ ክህነት ጽ/ቤት፣ አህጉረ ስብከት የሚገኙበትን ወቅታዊ ኹኔታ በመዳሰስ የሐዋርያዊ ተልእኮ አቅማቸውን ለማጎልበት የሚረዳ ሀገር አቀፍ ሥምሪት ሊያካሒድ ነው፡፡

ሥልጠናንና ግምገማን ያካተተው ይኸው ሀገር አቀፍ ሐዋርያዊ ሥምሪት፣ ከነገ ሰኔ 4 እስከ 6 ቀን 2010 ዓ.ም. ድረስ ለሦስት ቀናት የሚቆይ ሲኾን፤ በጠቅላይ ጽ/ቤቱ የመምሪያ ሓላፊዎች በሚመሩና ለየአህጉረ ስብከቱ በተመደቡ ከ90 ያላነሱ ልኡካን እንደሚከናወን ተገልጿል፡፡

ለሥልጠናው፣ስምንትያህል ዐበይት ጉዳዮች ተለይተው በሚመለከታቸው መምሪያዎች ማኑዋሎች መዘጋጀታቸው ተጠቅሷል፡፡ ለአራተኛ ጊዜ የተሻሻለው የቃለ ዐዋዲ መተዳደርያ ደንብና የሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤን በየደረጃው ማጠናከር፤ ስብከተ ወንጌል እና የዕቅበተ እምነት(የፀረ ፕሮቴስታንታዊ ተሐድሶ) እንቅስቃሴ፤ የሰንበት ት/ቤቶችን በየአጥቢያውና የሰንበት ት/ቤቶችን አንድነት በየደረጃው ማዋቀርና ማጠናከር፤ መልካም አስተዳደር እና የግጭት አፈታት ስልቶች፤ የዘመናዊ ሒሳብ አመዘጋገብና አያያዝ፤ የንብረት አመዘጋገብና አያያዝ እንዲሁም የቅርስ አያያዝና ቱሪዝም፣የሚሉት ሥልጠናው የሚያተኩርባቸው አርእስት ናቸው፡፡

ሥልጠናዊ ጉባኤው፣ በየአህጉረ ስብከቱ ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት የሚመራ ሲኾን፤ የመንበረ ጵጵስና ሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤ አባላት፣ የአህጉረ ስብከት ሥራ አስኪያጆች፣ የወረዳ ሊቃነ ካህናት፣ የሰበካ ጉባኤ እና የሰንበት ት/ቤት ክፍሎች ሓላፊዎች፣ ከከተማው አጥቢያ አብያተ ክርስቲያናት የተወከሉ ዐሥር፣ ዐሥር ማኅበረ ካህናት፣ ከ7 እስከ 10 የሰንበት ት/ቤት አባላት ይሳተፉበታል፤ ተብሏል፡፡

ከሥምሪቱ ቀደም ሲል፣ ግንቦት 29 እና 30 ቀን 2010 ዓ.ም.፣ለተሳታፊ ልኡካን፣ በማኑዋሎቹ ላይ የአሠልጣኞች ሥልጠና በየመምሪያ ሓላፊዎቹ እንደተሰጠና ሰፊ ውይይትም እንደተደረገበት ጠቅላይ ጽ/ቤቱ ገልጿል፡፡ በአህጉረ ስብከቱ የሐዋርያዊ ተልእኮ ኹለንተናዊ እንቅስቃሴ፣ የጎደለውንና የተጣመመውን በሥልጠናው ለይቶ መሙላትና ማቃናት ከጠቅላይ ጽ/ቤቱ እንደሚጠበቅ፣ብፁዕ ዋና ሥራ አስኪያጅ አቡነ ዲዮስቆሮስ በሥልጠናው ማጠቃለያ ላይ በሰጡት የቃል መመሪያ ተናግረዋል፡፡

በሥልጠናው አሰጣጥ፣ በማኑዋሎቹ መነሻነት፣ቤተ ክርስቲያንን በሚጠቅም መልኩ ነጻ፣ ግልጽና አሳታፊ ውይይት እንዲካሔድ ማድረግ ከልኡካኑ እንደሚጠበቅ ያሳሰቡት ብፁዕ ዋና ሥራ አስኪያጁ፣ የአህጉረ ስብከቱን ትክክለኛ ወቅታዊ ገጽታ ጠቅላይ ቤተ ክህነቱ በቅርበት ተገኝቶ የሚረዳበት እውነተኛና የተሳካ ተልእኮ ለማድረግ እንደሚያገለግል አስገንዝበዋል፡፡

“ተስፋ ወደፊት ነው፤ ታሪክ ወደኋላ ነው፤”ያሉት ብፁዕነታቸው፣በመንግሥት ሥርዐት ለውጡ ቀደምት አደራጆች ቤተ ክርስቲያንን የታደጉበት የሰበካ ጉባኤ ርእይ ብዙ ተጋድሎ እንደሚጠይቅ አመልክተዋል፡፡ ሀገር አቀፍ ሐዋርያዊ ሥምሪቱ፣ በሰበካ ጉባኤ ምሥረታ ዓመታት፣ በየአህጉረ ስብከቱ መዋቅሩን ለማስተዋወቅና ለመዘርጋት፣ በየጥሻው እያደሩ በብዙ ደክመው ያለፉትንና ስማቸውን ከመቃብር በላይ በተጋድሏቸው የጻፉትን እንደ ሊቀ ጉባኤ አባ አበራ በቀለ ያሉ አደራጅ አባቶቻችንን የሚያዘክረን እንደኾነ አስታውሰዋል፡፡

ቤተ ክርስቲያናችን የጊዜውን ፈተና ተቋቁማ ዘመን ተሻጋሪ ትኾን ዘንድ፣ ልኡካኑም በሐዋርያዊ ሥምሪቱ የሚያከናውኑት ተግባር የራሱ አስተዋፅኦ ያለው በመኾኑ፣በሙሉ አቅማቸው እንዲሠሩ አሳስበዋቸዋል – “ቤተ ክርስቲያን እየተጎዳች ነች ያለችው፤ ዘመን ቀድሞናል፤ እንድረስላት፤ አኹኑኑ ከባነንን መድረስ ይቻላል፤” ብለዋቸዋል፡፡

ሀገር አቀፍ ሐዋርያዊ ሥምሪቱ ስኬታማ እንዲኾን በቃለ ምዕዳናቸው የባረኩት ብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርክ አቡነ ማትያስ በበኩላቸው፣ በየአህጉረ ስብከቱ ሰበካ ጉባኤን በማጠናከርና ስብከተ ወንጌልን በማስፋፋት ረገድ ያሉብን ማነቆዎች ታውቀው መፍትሔ ለመስጠት የሚያስችል በመኾኑ፣ ልኡካኑ ተልእኳቸውን በአግባቡ እንዲወጡ አባታዊ መመሪያ ሰጥተዋል፤ “ጠቅላይ ሚኒስትሩ [ሌብነትን ስለማውገዝ]ያሉትንም አስተምሩበት፤” በማለትም አክለዋል፡፡

ሥምሪቱ፣ከሥልጠና ባሻገር፣የአህጉረ ስብከቱ ዓመታዊ የሥራ ክንውን በቢሮና በመስክ የሚገመገመምበትን መርሐ ግብር ያካተተ ሲኾን፤ በሰነዶች(ቅጾችና ሞዴሎች) እንዲሁም በራስ አገዝ ልማት ባደረጓቸው እንቅስቃሴዎች ይመዘኑባቸዋል፤ በአፈጻጸም ያጋጠሟቸውን ችግሮችና ቀጣይ ዕቅዶቻቸውንም ያስታውቁባቸዋል፡፡ ከሥምሪቱ መልስ፣ ኹሉም ልኡካን ሥልጠናውንም ግምገማውንም ያጠቃለለ ሪፖርት ለጠቅላይ ጽ/ቤቱ ያቀርባሉ፤ “በእኛ ደረጃ መታየትና መፈታት ያለበትን እንወስናለን፤ የቅዱስ ሲኖዶስን አመራር የሚሹትንም ለይተን እናቀርባለን፤” ብለዋል ብፁዕ ዋና ሥራ አስኪያጁ፡፡

በመንበረ ፓትርያርኩ የሰበካ ጉባኤ ማደራጃ መምሪያ ዋና አስፈጻሚነት የሚከናወነው ሀገር አቀፉ ሐዋርያዊ ሥምሪት በየዓመቱ በመደበኛነት መካሔድ ያለበት ቢኾንም፣ በትኩረትና የበጀት አቅም ማነስ ሳቢያ ለብዙ ጊዜያት ተስተጓጉሎ ቆይቷል፡፡የዘንድሮውም ሥምሪት ታቅዶ የነበረው በጥር ወር እንደነበርና በሀገራችን ልዩ ልዩ አካባቢዎች በነበረው የጸጥታ መደፍረስ እስከ አኹን መዘግየቱ ተገልጿል፡፡

ቀጣይነቱ አጠያያቂ ባይኾንም፣የሥምሪት ማኑዋሎች ዝግጅት በቂ ጊዜ ተሰጥቶት አግባብነት ባላቸው ባለሞያዎች ሊገመገምና የአሠልጣኝ ልኡካኑ አቅምም ሊጤን እንደሚገባ ተጠቁሟል፡፡ በአንዳንድ መምሪያ ሓላፊዎች የተሰናዱ ማኑዋሎች ወቅታዊነት እንደሚጎድላቸውና ከልኡካኑም መካከል በዕድሜና ተጓዳኝ ምክንያቶች የማሠልጠኛ ሰነዶቹን(በተለይም የሒሳብ አያያዝንና አመዘጋገብን ከነጠላ ወደ ኹለትዮች ስለማሸጋገር በተመለከተ) ለመረዳት ውስንነት የታየባቸው እንደነበሩ፣ በቅድመ ዝግጅቱ የአሠልጣኞች ሥልጠና መርሐ ግብር ወቅት ለመታዘብ መቻላቸውን ተሳታፊዎች ይናገራሉ፡፡

“በየዓመቱ መተያየቱ፣ መቃኘቱና መወያየቱ በራሱ ቀላል ነገር አይደለም፤ ነገር ግን ከሰው እጥረት ጀምሮ ጥቂት የማይባሉ መምሪያዎች የማኑዋል ወቅታዊነትና ከተልእኮው አስፈላጊነት አኳያም የልኡካኑ ብቃት ሊገመገም ይገባል፤ቅድመ ዝግጅቱና የልኡካኑ አቅም፣ “ቤት ያፈራው” ቢኾንም፣ ሊታሰብበት ይገባል፤ አልያ ቀረ እንዳይባል ያህል ዘልማዳዊ ብቻ ነው የሚኾነው፤” ይላሉ፡፡


በብዛትም በአቅምም የሰው ኃይል እጥረትና ውስንነት መኖሩን ያልሸሸጉት የጠቅላይ ጽ/ቤቱ ምንጮች፣ በሥምሪቱ የሚሳተፉ ልኡካን ምደባ የተደረገው፣ ኮሚቴ ተቋቁሞ ተመልምለው ከቀረቡ በኋላ በትምህርት ዝግጅታቸውና በሥራ ልምዳቸው የተሻሉትን በመምረጥ መኾኑን አስረድተዋል፡፡ እያንዳንዱ ልኡክ በአፈጻጸም የነበረውን አቅምና ተልእኮውን በአግባቡ ስለመወጣቱ አህጉረ ስብከቱ የታዘቡትን በሪፖርት ለጠቅላይ ጽ/ቤቱ የሚልኩ በመኾኑ፣ሥምሪቱን በሒደት እያጠናከሩ ለማስቀጠል ያግዛል፤ተብሏል፡፡

2 thoughts on “የጠቅላይ ቤተ ክህነት ጽ/ቤት: ዓመታዊውን ሀገር አቀፍ ሐዋርያዊ ሥምሪት ያካሒዳል

  1. Dave June 15, 2018 at 3:29 am Reply

    ጠ.ሚ አብይ እያደረጉ ላሉት ለውጥ እያመሰገንን እና በለውጡ እንዲቀጥሉ እያበረታታን፤፤ ቤተክርስቲያን የተወረሱባትን ሁሉም ሕንፃዎችና ንብረቶች እንዲመልሱላት በፍቅርና በትህትና ልንጠይቅ ይገባል፤፤

    ከሚገኘውም ገቢ ቤተክርስቲያን ህፃናት ማስደጊዎች፤ ትምህርት ቤቶች፤ ሆስፒታሎች፤ ክልኒኮች፤የእካልና የአቅም ውስንነት ያለባቸውን ወገኖች መገንቢያ ለታውለው ይገባል፤፤ ሌቦችና ዘረኞችም ከቤትክርስትያ መስተዳድር ወስጥ እንዲወጡ ግፍት ልናደርግ ይገባል፤፤

    ጠሚ አብይ እያደረጉ ላሉት ለውጥ እያመሰገንን እና በለውጡ እንዲቀጥሉ እያበረታታን፤፤ ቤተክርስቲያን የተወረሱባትን ሁሉም ሕንፃዎችና ንብረቶች እንዲመልሱላት በፍቅርና በትህትና ልንጠይቅ ይገባል፤፤ ከሚገኘውም ገቢ ቤተክርስቲያን ህፃናት ማስደጊዎች፤ ትምህርት ቤቶች፤ ሆስፒታሎች፤ ክልኒኮች፤የእካልና የአቅም ውስንነት ያለባቸውን ወገኖች መገንቢያ ለታውለው ይገባል፤፤

    ሌቦችና ዘረኞችም ከቤትክርስትያ መስተዳድር ወስጥ እንዲወጡ ግፍት ልናደርግ ይገባል፤፤

  2. Pafulvio.Com June 21, 2018 at 10:10 pm Reply

    In the absence of a higher authority to regulate the business, players are held accountable to
    an implied good faith contract.

Leave a comment