ሰበር ዜና – የምዕራብ ጎጃም ሀ/ስብከት ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ቶማስ ዐረፉ

ብፁዕ አቡነ ቶማስ፤ የምዕራብ ጎጃም(ፍኖተ ሰላም) ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ

ብፁዕ አቡነ ቶማስ የምዕራብ ጎጃም – ፍኖተ ሰላም ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ (፲፱፻፴፭ – ፳፻፮ ዓ.ም.)

የምዕራብ ጎጃም – ፍኖተ ሰላም ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ቶማስ ትላንት መጋቢት ፲፮ ቀን ፳፻፮ ዓ.ም. ምሽት 2፡00 ገደማ ዐርፈዋል፡፡

ብፁዕነታቸው የስኳር ሕመምተኛ እንደነበሩና እስካለፈው ዓመት ነሐሴ ወር ድረስ በቡሬ ቅዱስ ጊዮርጊስ ክሊኒክ ሕክምናቸውን ሲከታተሉ እንደቆዩ የሀገረ ስብከቱ ምንጮች ገልጸዋል፡፡

ለከፍተኛ ሕክምና ወደ አዲስ አበባ መጥተው በቅዱስ ገብርኤል ሆስፒታል የደም ማጣራት(ዲያሊስስ) ሲደረግላቸው የሰነበቱ ቢኾንም ጤናቸው መሻሻል ባለማሳየቱ ባለፈው ሳምንት ረቡዕ ከሆስፒታሉ በአምቡላንስ ወጥተው በኦክስጂን እየተረዱ ወደ ሀ/ስብከታቸው ከተመለሱ በኋላ ትላንት ምሽት 2፡00 ላይ በ71 ዓመታቸው (፲፱፻፴፭ – ፳፻፮ ዓ.ም.) ማረፋቸው ታውቋል፡፡

በሦስተኛው ፓትርያርክ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ተክለ ሃይማኖት አንብሮተ እድ በግንቦት ወር ፲፱፻፸፱ ዓ.ም. ከተሾሙት ኤጲስ ቆጶሳት አንዱ የነበሩት ብፁዕነታቸው ከ፳፻፬ ዓ.ም. ከነበሩበትና ካረፉበት ከምዕራብ ጎጃም – ፍኖተ ሰላም ሀ/ስብከት አስቀድሞ በሊቀ ጵጵስና ከመሯቸው አህጉረ ስብከት መካከል የድሬዳዋና ምዕራብ ሐረርጌ፣ የሰሜን ኦሞና ደቡብ ኦሞ የወለጋ፣ የአሶሳ እና የሰሜን ምዕራብ ሸዋ – ሰላሌ አህጉረ ስብከት ይገኙበታል፡፡

በፊት ስማቸው መልአከ ሣህል አባ መዘምር ተገኝ የሚባሉት ብፁዕ አቡነ ቶማስ÷ ጸዋትወ ዜማን፣ ቅኔን፣ መጻሕፍተ ሓዲሳትንና መጻሕፍተ ሊቃውንትን ከተለያዩ መምህራን በመገብየትና ዕውቀታቸውን በማስፋፋት ተጠያቂ መምህርና ሊቅ ለመኾን በቅተዋል፡፡

በመጻሕፍተ ሐዲሳትና መጻሕፍተ ሊቃውንት ትርጓሜያትና በቅዳሴ መምህርነታቸው የሚታወቁት ብፁዕ አቡነ ቶማስ፣ የሊቃውንት ጉባኤ፣ የስብከተ ወንጌልና ሐዋርያ ተልእኮ መምሪያዎችን በበላይ ጠባቂነት፣ በቅድስት ሥላሴ መንፈሳዊ ኮሌጅ በሃይማኖተ አበው መምህርነትና በሰዋስወ ብርሃን ቅዱስ ጳውሎስ መንፈሳዊ ኮሌጅ በዲንነት አገልግለዋል፤ የታዕካ ነገሥት በዓታ ለማርያምንና የመንበረ መንግሥት ቅዱስ ገብርኤል ገዳማትን በበላይ ሓላፊነት አስተዳድረዋል፡፡

ትምህርተ ሃይማኖትን የሚከበውን ቃለ ስብከታቸውንም ‹‹ፍኖተ እግዚአብሔር›› በሚል ርእስ በመጽሐፍ አሳትመዋል፤ በሀ/ስብከታቸውም በፈለገ ሰላም ቅ/ጊዮርጊስ ቤተ ክርስቲያን የአብነት ትምህርት በተለይም የመጽሐፍ ትርጓሜ ቤተ ጉባኤ ሊቃውንትን አግኝቶ ደቀ መዛሙርት አብዝቶ እንዲጠናከርና እንዲስፋፋ በብዙ ደክመዋል፡፡

የአምስተኛውን ፓትርያርክ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ጳውሎስን ዕረፍት ተከትሎ ‹‹ከፓትርያርክ ምርጫው በፊት የአባቶች ዕርቀ ሰላም(ሲኖዶሳዊ ዕርቅ) ይቅደም›› የሚሉ ድምፆች ጎልተው በተሰሙባቸው ወራት ነፍስ ኄር ብፁዕ አቡነ ቶማስ ለቤተ ክርስቲያን አስተዳደራዊ አንድነት ከደከሙ ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት ጋራ መንፈሳቸውንና አቋማቸውን አስተባብረዋል፤ አራተኛው ፓትርያርክ ብፁዕ ወቅዱስ  አቡነ መርቆሬዎስ ወደ አገር ቤት ተመልሰው በመንበሩ መቀመጥ እንደሚገባቸውም ሳያሰልሱ ይናገሩ እንደነበር የወቅቱን አሰላለፍ ባቀረብንበት ዘገባችን ማስነበባችን ይታወሳል፡፡

ትምህርተ ሃይማኖትን አስኳል ባደረገው ጣዕመ ስብከታቸው፣ ለሰባክያነ ወንጌል ሥልጠና ቀዳሚ ባደረገው አመራራቸው፣ ክብረ ክህነትን ሲያስጠብቁ ብዙ መከራ በተቀበሉበት ቃለ ተግሣጻቸውና ለልማት ትኩረት በሰጠው የተግባር አርያነታቸው የሚታወሱት የብፁዕነታቸው የቀብር ሥነ ሥርዓት ነገ፣ መጋቢት ፲፰ ቀን ፳፻፮ ዓ.ም. ብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርክ አቡነ ማትያስና ዐሥራ አንድ ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት በተገኙበት በዚያው በፍኖተ ሰላም ፈለገ ሰላም ቅዱስ ጊዮርጊስ ቤተ ክርስቲያን ከቀኑ በ9፡00 ሰዓት እንደሚከናወን ተገልጧል፡፡

አምላከ ቅዱሳን እግዚአብሔር የብፁዕ አባታችንን ነፍስ ከማኅበረ ቅዱሳን ይደምርልን፡፡

************************************************

ኦ አባ ንበር በማዕከሌነ
በወርኃ መጋቢት በአዝመራው ወቅት ተጠራ
ለዘመናት ወንጌል ዘርቶ የብዙኃንን ልብ ያበራ
እውነትም ብፁዕ ቶማስ ትጉህ የፍቅር አርበኛ
የመተሳስብ የሰላም የአንድነት አባት ዳኛ
የቀለም ራስ መምህር የመጻሕፍት ቌት ጠንቃቂ
ጎባጣውን የሚያቀና የተጣመመውን ሐራቂ
እንደሰው መጠን ቢፈጠር አዳማዊ ቢኾን ፍጥረቱ
ፍጹም አስደንጋጭ ኾነብን አራደን የቶማስ ሞቱ

ዲያቆን ዘፍጽምና ካህን መናኝ መነኩሴ
መምህር ወጳጳስ ኀሩይ በኀበ ሥላሴ
የቅዳሴው አበጋዝ መራሒ ወንጌል አንደበቱ
እንደምን ድካም ያዛቸው እንደምንስ ተረቱ
የተዋሕዶን ክብር ዝና በዓለም መደረክ ያገዘፈ
በመክሊቱ የሠራበት እልፍ አእላፋትን ያተረፈ
ንዋየ ኀሩይ ቶማስ የታላቅነት ማሳያ
ብርሃን ለምግባር ሠናይ የመልካምነት ገበያ

በመንፈሳዊ ጥበብ የጠለቀ በያሬዳዊ ዜማ የናኝ
እምነትና ፍልስፍናን በዕውቀት ቀንበር ያቆራኘ
ኦ አባ ትጉህ ለጸሎት ኃያል ጽኑ ለተጋድሎ
ያስመሰከረ ማንነቱን በጉባኤ ቤት አውድማ ውሎ
እጨጌ ለመንበረ ፍኖተ ሰላም አቡነ
ሊቀ ጳጳስ ዘጎጃም በታቦተ ጽዮን እምነ
ሥዩመ እግዚአብሔር ወሰብ የፍኖተ ሰላም መሪ
እንደ ፀሐይ ደማቅ እንደ ኮኮብም አብሪ
መዋቲ ሥጋ የለበሰ ሞት ዕጣው ቢኾንም ቅሉ
የአባት ሞት ግን መሪር ነው የማይታመን ለኹሉ

በወርኃ ፍጹም ሱባኤ መጋቢት ሐተታ
እምድኽ ፈለሰ ቶማስ ወደ ላይኛው ቦታ
መከራው ይበልጥ በረታ የሐዘን እንባ ዘነበ
አቡነ መምህር ቶማስ ውስተ መቃብር ሰከበ
ጆሯችንን ጭው ያደረገ ፍጹም ለማመን የከበደ
አባ ሞትኽን ሰማን ልባችን በሐዘን ራደ

እግዚአብሔር ያጽናሽ ቤተ ክርስቲያን
ቅኔ፣ ጾመ ድጓ፣ መዋስዕት ምዕራፉን
ጠንቅቆ ያወቀ ዝማሬ ድጓውን
የአበውን ትውፊት በደንብ የቀሰመ ልጅሽን ሞት የነጠቀሽ
ሌት እና ቀን ለመምሰል ሳይኾን በመኾን ያቆመሽ
ስምኽ ከመቃብር በላይ ያበራል ጸንቶ እንደፋና
የወንጌል አርበኛው ቶማስ የሔድክ በጽድቅ ጎዳና
የወንጌል ብርሃን ባልበራበት ከአጽናፍ አጽናፍ ዞሮ
ምንኩስና ጵጵስናን በሕይወቱ በእውነት ኖሮ
ነዳያንን በፍቅር ስቦ ምስኪናን በችሮታ
ሰብስቦ ያኖረው ክንድኽ ዛሬስ እንደምን ተረታ

ጸዐዳው የሕይወት መምህር የቀለም ገበሬ
የኹለት ዓለሙን ምሁር ሞት እጁን ያዘው ዛሬ
የአብርሃም እቅፍ ለአንተ የገነት በር ይከፈት
በገድል ትጋት የኖረችው ነፍስም ታግኝ ዕረፍት
ተዋናይ በመንፈስ አባ ንበር በማዕከሌነ
ሳህል ወጸልይ ምሕረት ሀበ ማርያም እምነ
ሊቀ ጳጳሳት ዘሀገረ አባ ኢትዮጵያ
ከአትሮንሱ ላይ ተነሣ ታጠፈ የዕውቀት ገበያ
በትረ ሙሴ ይዞ ሕዝቡን በጥበብ የመራ
ይኽው ወር ተራ ደርሶት እርሱም በመጋቢት ተጠራ
ሕይወታቸው ያለው አይታበልምና ቃሉ
ብፁዕ አቡነ ቶማስ ያክብርህ ከሃሌ ኵሉ፡፡

ከመምህር ሳሙኤል አያልነህ
መታሰቢያነቱ መጋቢት 16 ቀን 2006 ዓ.ም.
በመሞት ለተለዩን ለብፅዕ አቡነ ቶማስ ሊቀ ጳጳስ

25 thoughts on “ሰበር ዜና – የምዕራብ ጎጃም ሀ/ስብከት ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ቶማስ ዐረፉ

  1. Anonymous March 26, 2014 at 9:58 am Reply

    Nefsachewin bekibir yanurilin!!!

  2. Anonymous March 26, 2014 at 11:48 am Reply

    Ye abatachinin Nefes yimarilin!!!!! Degage abatoch siyalefu yasferal!!!!!

  3. Anonymous March 26, 2014 at 12:34 pm Reply

    እግዚአብሄር አምላክ ነብሳቸውን በህፅነ አብርሃም ያኑራት

  4. Anonymous March 26, 2014 at 1:05 pm Reply

    Egziabher Nebsachewin begenet yanurlin

  5. Anonymous March 26, 2014 at 1:33 pm Reply

    bewnwt nefisachewun begent keqidusan yedemirilin!

  6. Anonymous March 26, 2014 at 3:30 pm Reply

    አምላከ ቅዱሳን እግዚአብሔር የብፁዕ አባታችንን ነፍስ ከማኅበረ ቅዱሳን ይደምርልን፡፡

  7. Anonymous March 26, 2014 at 3:36 pm Reply

    Mehara Nefsomu leabune tomas! yihdir berketke laeliye wolaile kulomu kirstiyan oo abuye thomas!

  8. Anonymous March 26, 2014 at 6:09 pm Reply

    የ አባታችንን ነፍስ እግዚአብሔር ይማር !!!ነፍሳቸውንም ከ ማኅበረ ቅዱሳን ይደምርልንን ::በጎ የሚሰራ እየበረከተ አይደለምና ለቤተክርስቲያናችን ማልቀስ ይገባናል ::እግዚአብሔር ቤተክርስቲያናችንንና ሀገራችን ይጠብቅልን ::

  9. Anonymous March 26, 2014 at 6:20 pm Reply

    Egziabher nefsachewun bemengste semayat yanurln

    • Anonymous March 26, 2014 at 8:49 pm Reply

      egziabhier nefsachewn begenet yanur

  10. Adane March 26, 2014 at 11:03 pm Reply

    እግዚአብሔር አምላክ ነፍሳቸውን በገነት ያኑርልን። ለእኛም በረከታቸው ይደርብን።

  11. Anonymous March 26, 2014 at 11:34 pm Reply

    ኦ አባ ንበር በማዕከሌነ!

  12. Anonymous March 27, 2014 at 5:26 am Reply

    አምላከ ቅዱሳን እግዚአብሔር የብፁዕ አባታችንን ነፍስ ይደምርልን፡፡

  13. Anonymous March 27, 2014 at 6:07 am Reply

    እድሜዎትን በሙሉ ያመለኩት ያገለገሉት አምላክ ነፍሶትን በገነት ያኑርልን !!

  14. Anonymous March 27, 2014 at 6:27 am Reply

    Amlake kidusan yetalakun abat nefs yimarlin. bereketachew yidresen!!!

  15. Anonymous March 27, 2014 at 7:32 am Reply

    አቡነ ቶማስ

    ብፅዑ አባታችን የወንጌል ገበሬ
    ለመንጋው አሳቢ ያበቡ በፍሬ
    በስጋ ተለዩን ቀኑ ደርሶ ዛሬ::

    አርአያ ክህነት ጸሎት ስብከታቸው
    መስታወት ለሁሉ ጥልቁ ትምህርታቸው
    አርምሞ እርጋታ ፀጥ ያለ ኑሮአቸው
    በትንሽ ንግግር ማራኪ ምክራቸው
    የትህትና አባት የፍቅር የሰላም
    የምግባር ፍሬያቸው መቼም አይረሳም፡፡

    ለማኅበረ ሰላም ባለውለታችን
    መካሪ አስተማሪ መንገድ አሳያችን
    ለአገልግሎት ውጡ በሰላም ጎዳና
    መከሩ ብዙ ነው ጌታ ብሏልና
    ‹‹ ማኅበረ ሰላም ›› በማለት ሰይመው
    ወደ ወንጌል መሩን ባርከውን መርቀዉ ፡፡

    ሃዘኑ ጥልቅ ነው ከልብ የማይወጣ
    መካሪ ዘካሪ ተቆጪ ስናጣ
    የእርስዎን አደራ መቼም አንረሳም
    ከአገልግሎት መንገድ ከቶ አንወጣም
    በዘመን ዳርቻ ከኛ ቢለዩንም
    ፍሬዎ ያብባል እስከዘለዓለም፡፡

    ሰው በሕይወት ዘመኑ ፈጣሪን አክብሮ
    ሃይማኖት ከምግባር በእውነት አስተባብሮ
    ከኖረ በምድር በፍቅር በትጋት
    ተስፋይቱ ገነት በእውነት የእርሱ ናት፡፡

    ጸሎት ቡራኬዎ አሁንም ይድረሰን
    የእርስዎን በረከት ፈጣሪ ያሳትፈን
    በመንግስተ ሰማይ በማታልፈው ቦታ
    ነፍስዎን ያኑራት የሠራዊት ጌታ፡፡

    ከውዳሴ አባት / መጋቢት 18,2006 /

  16. Anonymous March 27, 2014 at 9:03 am Reply

    Amlak nefisachewun yimarlin!!!!!!!!!!!!!!!!!!!!!!!!!!

  17. Anonymous March 27, 2014 at 9:08 am Reply

    May God rest his soul in the kingdom of Heaven,

  18. berhan March 27, 2014 at 10:29 am Reply

    bewnet abatacen betam liq nberu betam awqacewalew GETA MDHANYALEM nbesacewn bmengestsmayat yanureln AMEN

  19. Anonymous March 27, 2014 at 11:33 am Reply

    May God rest the soul of our True father in Kingdom of Heaven!

  20. Anonymous March 27, 2014 at 12:48 pm Reply

    እግዝአብሄር ነብሳቸውን ይማር!!!

  21. Habtemariam March 27, 2014 at 7:22 pm Reply

    let his soul rest in peace and let his prayer be on us.

  22. Anonymous March 27, 2014 at 9:46 pm Reply

    በረከታቸው ይደርብን ! አሜን

  23. Anonymous March 28, 2014 at 9:05 am Reply

    እግዚአብሔር ነፍሳቸውን ይማር፤እኛንም በቸርነቱና በረደታቸው ይጠብቀን!

  24. wudetaw libassie March 28, 2014 at 9:07 am Reply

    እግዚአብሔር ነፍሳቸውን ይማር፤እኛንም በቸርነቱና በረደታቸው ይጠብቀን!

Leave a comment