የምእመናን ቆጠራና ምዝገባ በአህጉረ ስብከት ሓላፊነት ይካሄዳል: የቅ/ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ ስብሰባ መግለጫ

  • ቅ/ሲኖዶስ ስለ ኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ታሪካዊነትና ቀዳሚነት እውነታውንና ትክክለኛውን የሚገልጽ ጽሑፍ እንዲዘጋጅ ለሊቃውንት ጉባኤው ትእዛዝ ሰጠ
  • የኢትዮጵያ ቴሌቪዥንና ሬዲዮ ድርጅት ለምልአተ ጉባኤው ስብሰባ የሰጠው ሽፋን ‹‹የጉርሻ ያህል ነው›› በሚል ተነቀፈ
  • ‹‹ጉባኤው አገር አቀፍ ብቻ ሳይኾን ዓለም አቀፍም ነው፤ የምንሰጠው ትምህርት ነው፤ የምንወድቀው የምንነሣው ስለ ሀገር ጉዳይ ነው፤ ቤተ ክርስቲያን በዐይን የሚታይ በእጅ የሚጨበጥ ታሪክ ነው ያስረከበችው፤ በምን ምክንያት ነው [የአየር ሽፋኑ]ቀለል የሚለው›› /ብፁዕ አቡነ ቄርሎስ/
  • ‹‹ከባለሥልጣናት[ከመንግሥት] የምናገኛቸውን መልእክቶች እናስተላልፋለን፤ ከጤና ጥበቃ ሚኒስቴር ሚኒስትሩ እናቶች በሆስፒታል እንዲወልዱ ደጋግማችኹ አስተላልፉን ብለው ነግረውን በቤተ ክርስቲያናችን ብዙ ሺሕ ሕዝብ በተሰበሰበበትና በየአጋጣሚው እናስተላልፋለን፤ እኛም እዚህ ስለ አገር ጉዳይ እንነጋገራለን፤ የምንነጋገረው ግን የሚተላለፈው የጉርሻ ያህል ነው፤ ለሕዝቡ እንዲተላለፍ እንጂ የሚዲያ ሱሰኛ ኾነን አይደለም፤ የሚነገረው ነገር ለሕዝቡ በአግባቡ ቢተላለፍ መልካም ነው›› /ብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርክ አቡነ ማትያስ/

Holy SynodTikmit Meeting

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ምእመናን ቆጠራና ምዝገባ በእያንዳንዱ አህጉረ ስብከት ሓላፊነት እንደሚካሄድ ቅዱስ ሲኖዶስ አስታወቀ፡፡

‹‹ቤተ ክርስቲያን በሥሯ ያሉ ምእመኖቿን ቆጥራ መመዝገብ እንድትችል›› የሚካሄደው ይኸው ታላቅ አገራዊ ክንዋኔ የሰበካ ጉባኤ ማደራጃ መምሪያ በሚያዘጋጀው ቅጽ አማካይነት እንደሚከናወን ነው ቅዱስ ሲኖዶሱ የገለጸው፡፡

የመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተ ክህነት ሰበካ ጉባኤ ማደራጃ መምሪያ በ፳፻፮ ዓ.ም. በጀት ዓመት የምእመናን ቆጠራ ለማካሄድ ከብር 29 ሚልዮን በላይ የበጀት ጥያቄ ለቅ/ሲኖዶስ ሲኖዶስ ጽ/ቤት ማቅረቡን መዘገባችን የሚታወስ ሲኾን ዛሬ በቅ/ሲኖዶሱ መግለጫ እንደተጠቀሰው፣ በአህጉረ ስብከት ሓላፊነት የሚካሄደውን ቆጠራ ክንውን በቀጣይ የምንመለከተው ይኾናል፡፡

በተያያዘ ዜና፣ ስለ ኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ታሪካዊነትና ቀዳሚነት ሁሉም ሰው መጻፍ ሲገባው እውነት ያልኾነውን፣ በማስመሰል የሚነገረውንና የሚጻፈውን ማስተካከል እንደሚያስፈልግ ቅዱስ ሲኖዶሱ አሳስቧል፡፡

በመኾኑም እውነተኛውንና ትክክለኛውን አስተካክሎ ለሕዝብ፣ ለትውልደ ትውልድ ማስተላለፍ እንዲቻል መነሻ ይኾን ዘንድ በብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት የኮሚቴ አባልነት ተጠንቶ የቀረበውን ጽሑፍ ምልአተ ጉባኤው በንባብ ሰምቶ ጉዳዩ ወደ ሊቃውንት ጉባኤ እንዲቀርብ ትእዛዝ መስጠቱን ቅ/ሲኖዶሱ አስታውቋል፡፡

የቅዱስ ሲኖዶሱ መግለጫ እንደሚያመለክተው፣ ሊቃውንት ጉባኤው ስለ ኢትዮጵያ ታሪካዊነትና ጥንታዊነት በምልአተ ጉባኤው ላይ የተነበበውንና በብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት የተዘጋጀውን የመነሻ ጽሑፍ አብራርቶ፣ አስፍቶና አምልቶ ለግንቦት፣ ፳፻፮ ዓ.ም. የርክበ ካህናት ምልአተ ጉባኤ እንዲያቀርብ ተወስኗል፡፡

የቅዱስ ሲኖዶስ አባላት የኾኑ ሦስት ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት፡- ብፁዕ አቡነ ማርቆስ፣ ብፁዕ አቡነ ኄኖክ እና ብፁዕ አቡነ እንድርያስ በቅርቡ በተካሄደው ፴፪ው የመንበረ ፓትርያርክ አጠቃላይ ሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤ ዓመታዊ ስብሰባ ላይ፥ ኢትዮጵያ ከአይሁድ በፊት ጀምሮ በአምልኮተ እግዚአብሔር ጸንታ መኖሯን፣ ክርስትናም ወደ ኢትዮጵያ የገባው ክርስቶስ ባረገበት ዓመትና ቅዱሳን ሐዋርያት ገና ከኢየሩሳሌም ባልወጡበት በ፴፬ ዓ.ም. መኾኑን ጠቅሰው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያንን ታሪካዊነትና ቀዳሚነት በማስረዳት ከፌዴራል ጉዳዮች ሚኒስቴር ሓላፊዎች ጋራ መጠያየቃቸው ይታወሳል፡፡

የቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤው ጥቅምት ፲፩ ቀን ፳፻፮ ዓ.ም. በመክፈቻ ሥርዐተ ጸሎት የጀመረውንና ለዐሥር ቀናት ያህል ሲያካሂድ የቆየውን የመጀመሪያ ዓመታዊ የምልአተ ጉባኤ መደበኛ ስብስባ ዛሬ፣ ጥቅምት ፳፩ ቀን ፳፻፮ ዓ.ም. በጸሎት አጠናቋል፡፡

ምልአተ ጉባኤው መደበኛ ስብሰባውን ሲያጠናቅቅ ያወጣው ባለ28 ነጥብ መግለጫ የሚከተሉትን ዋና ዋና ነጥቦች አካትቷል፡-

  • ከአጥቢያ ቤተ ክርስቲያን እስከ አዲስ አበባ ሀ/ስብከት ጽ/ቤት ድረስ በባለሞያዎች ተጠንቶ የቀረበውና በስላይድ የታየው የሥራ መዋቅር ወደ ታች ወርዶ በካህናት፣ በምእመናንና በሰንበት ት/ቤት ወጣቶች ውይይት ዳብሮ በሚገባ ተጠንቶና ተስተካክሎ ለቋሚ ሲኖዶስ እንዲቀርብና ቋሚ ሲኖዶሱም አይቶና ተመልክቶ በሥራ ላይ እንዲያውል ምልአተ ጉባኤው ወስኗል፡፡
  • ቤተ ክርስቲያናችን ወደፊት የምታከናውነው ማኅበራዊና መንፈሳዊ አገልግሎት በዕቅድ የሚመራ እንዲኾን ለማስቻል በግንቦቱ ርክበ ካህናት ጉባኤ ፳፻፭ ዓ.ም. ተቋቁሞ የነበረው ኮሚቴ ያዘጋጀውን ጥናት ለጉባኤው አቅርቦ ጉባኤው ማብራሪያውን ካዳመጠ በኋላ ኮሚቴው ያላለቁ ሥራዎችን እንዲቀጥል በማለት መመሪያ ሰጥቷል፡፡
  • የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ጥንታዊትና ታሪካዊ እንደመኾኗ ኹሉ በቀጣይም አጠቃላይ ማኅበራዊም ኾነ መንፈሳዊ ሥራዎቿን በመሪ ዕቅድ በመምራት ሙስናና የመልካም አስተዳደር ዕጦትን ከሥሩ መቅረፍ እንዲቻል በባለሞያዎች የተጠናውን የመሪ ዕቅድ ዘገባ በመገምገም በቀጣይ ዕቅዱ ዳብሮ በሥራ መተርጎም በሚቻልበት ኹኔታ ተዘጋጅቶ እንዲቀርብ ጉባኤው መመሪያ ሰጥቷል፡፡
  • አሁን ያለው ሕገ ቤተ ክርስቲያን ተሻሽሎ እንዲቀርብ በተወሰነው መሠረት የተሻሻለው የሕገ ቤተ ክርስቲያን ረቂቅ የቅዱስ ሲኖዶስ አባላት እንዲመለከቱት የታደለ ሲኾን እንዲሁም በሚመለከታቸው ባለድርሻ አካላት ታይቶና ሐሳብ ተሰጥቶበት በ፳፻፮ ዓ.ም. ግንቦት ርክበ ካህናት ውይይት እንዲካሄድበት ምልአተ ጉባኤው ወስኗል፡፡
  • በውጭው ዓለም ገለልተኛ አብያተ ክርስቲያናት ነን በሚል የሚገኙ ወገኖች ወደ እናት ቤተ ክርስቲያናቸው እንዲመለሱ የቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ ጥሪውን ያስተላልፋል፡፡
  • በውጭ አገር ከሚገኙ የቤተ ክርስቲያን አባቶች ጋራ ተጀምሮ የነበረው ዕርቀ ሰላም ወደፊት እንዲቀጥልና የቤተ ክርስቲያኒቱ አንድነት እንዲጠናከር ጉባኤው ተስማምቷል፡፡
  • ገዳማቱን መልሶ ማቋቋምና ማጠናከር ብሎም በነበሩበት ኹኔታ አደራጅቶ ሥራቸውን መቀጠል ይችሉ ዘንድ የሚያመለክት በመምሪያው በኩል ሰፊ ጥናት የተደረገ በመኾኑ ገዳማቱ የሚገኙትም በየአህጉረ ስብከቱ ስለኾነና ብፁዓን አበው የሌሉበት ጥናትም አጥጋቢ ውጤት ስለማይኖረው የተወሰኑ ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት ከመምሪያው ተጠሪ ጋራ ተገናኝተው ገዳማቱ እንዴት መቋቋምና መልማት እንዳለባቸው ጥናት ይደረግበት በሚለው ጉባኤው ተስማምቶ ጠለቅ ያለ ሐሳብ ከነመፍትሔው አጥንተው ለግንቦት ፳፻፮ ዓ.ም. ርክበ ካህናት ምልአተ ጉባኤ እንዲያቀርቡ፡

1.  ብፁዕ አቡነ ኤጲፋንዮስየምዕራብ ሸዋ /ስብከት ሊቀ ጳጳስ፣
2.  ብፁዕ አቡነ ሳሙኤልየልማትና ክርስቲያናዊ ተራድኦ ኮሚሽን ሊቀ ጳጳስ፣ የሕንፃዎችና   ቤቶች አስተዳደር ድርጅት የበላይ ሓላፊ
3.  ብፁዕ አቡነ ቀሌምንጦስየከምባታ ሐዲያና ጉራጌ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ በመምረጥ ምልአተ ጉባኤው በሙሉ ድምፅ ተስማምቶ ወስኗል፡

  • የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በርካታ የሥነ ጽሑፍ፣ የሥነ ጥበብ፣ ሥነ ሥዕልና ኪነ ጥበብ ቅርሶችና ሀብቶች ባለቤት መኾንዋ የታወቀ ስለኾነ፣ የእነዚህ የቤተ ክርስቲያኒቱ የዜማ መጻሕፍት፣ የትርጓሜ መጻሕፍት፣ የሕንፃዎች፣ የቋንቋ በአጠቃላይም ብሔራዊው የአእምሮ ንብረት ባለቤትነት መብቷ በሕግ ይከበር ዘንድ በቅርስ ጥበቃና ምዝገባ በቤተ መጻሕፍት ወመዘክር መምሪያ  ተከታታይነት ጉዳዩ ለሚመለከተው የፍትሕ አካል ቀርቦ ውሳኔ እንዲያገኝ፤
  • የአብነት ትምህርት ቤቶችንና የካህናት ማሠልጠኛ ማእከላትን፣ በጥንታዊነታቸውና በታሪክ መዘክርነታቸው ዕውቅና ያላቸውን ገዳማት፣ አሳዳጊ አልባ ዕጓለማውታ ሕፃናት እየተማሩ የሚያድጉበትንና ሴቶች መነኰሳዪያት በምናኔ የሚኖሩባቸውን ገዳማት በበለጠ እንዲጠናከሩ ማድረግ የታመነበት ስለኾነ፣ ለዚሁ አገልግሎት የሚውል በጀት በቤተ ክርስቲያኒቱ ማእከላዊ አስተዳደር ተጠንቶ ይቀርብ ዘንድ ቅዱስ ሲኖዶስ ቀደም ሲል መመሪያን ሰጥቷል፤ አሁንም በድጋሚ መምሪያውን አጽንቷል፡፡
  • ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን በልማት ዘርፍ ዙሪያ የምታደርገው እንቅስቃሴ በማእከልም ኾነ በየአህጉረ ስብከቱ በበለጠ ተጠናክሮ እንዲቀጥል ምልአተ ጉባኤው ተስማምቷል፡፡
  • የቤቶችና ሕንጻዎች አስተዳደር ድርጅትን በተመለከተ በሚፈርሱ ቤቶች ምትክ ቸል ሳይባል በትጋትና በንቃት የመልሶ ማልማቱ የሕንጻ ግንባታ ለማካሔድ የሚያግዝ ገንዘብ ማግኘት እንዲቻል ለየአህጉረ ስብከት፣ ለአጥቢያ አብያተ ክርስቲያናትና በጠቅላይ ቤተ ክህነት ሥር ላሉ ድርጅቶች የአክስዮን ሽያጭ እንዲደረግ ተወስኗል፡፡
  • የቅድስት ሥላሴ መንፈሳዊ ኮሌጅ፣ የቅዱስ ፍሬምናጦስ አባ ሰላማ ከሣቴ ብርሃን መንፈሳዊ ኮሌጅ፣ የሰዋስወ ብርሃን ቅዱስ ጳውሎስ መንፈሳዊ ኮሌጅ የሦስቱም የቤተ ክርስቲያኒቱ መንፈሳውያን ኮሌጆች በጀታቸው ተጠቃሎ ወደ ጠቅላይ ቤተ ክህነቱ ገቢ እየኾነ በጀታቸውንም ጠቅላይ ቤተ ክህነቱ እየበጀተ እንዲከፍል ጉባኤው በሙሉ ድምፅ ወስኗል፡፡ ከዚህም ጋራ በቅድስት ሥላሴ መንፈሳዊ ኮሌጅ ሥር የሚተዳደረው ከኮሌጁ ጋራ ተያይዞ የሚገኘው አዲሱ ትልቁ ሕንጻ በጠቅላይ ቤተ ክህነት ቤቶችና ሕንጻዎች አስተዳደርና ልማት ድርጅት ሥር ኹኖ የሕንጻዎቹ ወርኃዊ የኪራይ ገቢም በሕጋዊ መንገድ እንዲሰበሰብ ቅዱስ ሲኖዶስ ወስኗል፡፡
  • በጥንታዊቷ፣ በታሪካዊቷ በርእሰ አድባራት ወገዳማት አክሱም ጽዮን ቤተ ክርስቲያን ዐውደ ምሕረት በመሠራት ላይ ያለው ቤተ መጻሕፍት ወመዘክሩ ግንባታን አስመልክቶ ከዓቢይ ኮሚቴው በቀረበው ሪፖርት ላይ በመነጋገር በቀጣይ የገቢ ማሰባሰቢያ ስልቶችን ያስቀመጠ ከመኾኑም በላይ ለጊዜው ለተቋራጩ ብር 5‚000‚000 (አምስት ሚልዮን ብር) እንዲሰጠውና የቆመው የግንባታ ሥራ እንዲቀጥል ወስኗል፡፡
  • የጣራ ቂርቆስ ገዳም አንጡራ ሀብት የኾነው መስቀለ ያሬድ ተሰርቆ ወደ ውጭ ተወስዶ ከቆየ በኋላ ወደ ሀገሩ ተመልሶ በመንበረ ፓትርያርክ ቤተ መጻሕፍት ወመዘክር ስለሚገኝ ገዳሙ መስቀሉ እንዲሰጠው በጽሑፍ በመጠየቁ እንዲሰጥ ምልአተ ጉባኤው ወስኗል፡፡
  • የመንበረ ጸባዖት ቅድስት ሥላሴ ካቴድራል ሕንጻ ከጊዜ ብዛት የተነሣ ውኃ በማስገባቱ እድሳት የሚያስፈልገው ስለኾነ የእድሳቱም ጥናት በመቅረቡ የካቴድራሉ ሕንጻ የቅድስት ቤተ ክርስቲያናችንና የሀገር ቅርስ እንዲሁም የቱሪስቶች መዳረሻ በመኾኑ የውስጥና የውጭ ቁመናው እንደያዘ በጥንቃቄ እድሳቱ እንዲደረግ ጉባኤው ወስኗል፡፡
  • የ፴፪ው አጠቃላይ ሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤ ውሳኔና የጋራ መግለጫ የ፳፻፮ ዓ.ም. የሥራ መመሪያ እንዲኾን በምልአተ ጉባኤው ጸድቋል፡፡
  • ስለ ሰንበት ት/ቤቶች ውስጠ ደንብ ተጠንቶ የቀረበው መመሪያ ጸድቆ በሥራ ላይ እንዲውል ተወስኗል፡፡
  • በቅዱስ ሲኖዶስ ውሳኔ ተጠንቶ እንዲቀርብ ስለታዘዘው የማኅበረ ቅዱሳን ደንብ ደንቡን እንዲያጠና የተመደበው ኮሚቴ ጥናቱ ለጊዜው ያልደረሰለት መኾኑን ስለገለጸ ለ፳፻፮ ዓ.ም. የግንቦት ርክበ ካህናት ምልአተ ጉባኤ ጥናቱ ተጠናቆ እንዲቀርብ ጉባኤው ትእዛዝ ሰጥቷል፡፡
  • በጉጂ ዞን ነገሌ ቦረናና የሲዳማ ዞን አህጉረ ስብከትን በተመለከተ በሁለት ተከፍለው ያለመግባባት ችግር ፈጥረዋል በሚል የተነሣው ሁከት ዓመታትን ካስቆጠረ በኋላ ችግሩን የፈጠሩት የሁለቱም ወገኖች ጉዳዩ በዕርቅ እንዲፈጸም ጥያቄ በማቅረባቸው የቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ የዕርቀ ሰላሙን ሂደት የተቀበለ በመኾኑ እቦታው ላይ ተገኝተው ዕርቀ ሰላሙን የሚያወርዱ ብፁዓን አባቶችን ሠይሟል፤

1.  ብፁዕ አቡነ ማትያስ – የካናዳ ሀ/ስብከት ሊቀ ጳጳስ፣
2.  ብፁዕ አቡነ እስጢፋኖስ – በአዲስ አበባ ሀ/ስብከት የብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርክ ረዳትና የጅማ ሀ/ስብከት ሊቀ ጳጳ
3.  ብፁዕ አቡነ ሉቃስ – የቅዱስ ሲኖዶስ ዋና ጸሐፊና በክልል ትግራይ የምዕራብ ሰቲት ሑመራ ሀ/ስብከት ሊቀ ጳጳሳት፤

በመኾን ስምምነቱንና ዕርቀ ሰላሙን አስፈጽመው የመጨረሻ የዕርቁን ሰነድ ለጉባኤው እንዲያቀርቡ ተወስኗል፡፡

 


                       

 

18 thoughts on “የምእመናን ቆጠራና ምዝገባ በአህጉረ ስብከት ሓላፊነት ይካሄዳል: የቅ/ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ ስብሰባ መግለጫ

  1. ገ/ሚካኤል October 31, 2013 at 2:57 pm Reply

    ሰናይ ውእቱ፡፡

    • selamm November 2, 2013 at 7:50 am Reply

      እግዚያብሔር አምላክ የኢትዮዽያን ቤተክርስቲያን ይጠብቃታል

  2. (መለሰ ዘነበወርቅ) October 31, 2013 at 5:23 pm Reply

    አምላክ የዚህችን ቤተክርስቲያን ችግር አይቶ የምእመኗንም እንባ አብሶ ሊያነሳት እንደሆነ ይሰማኛል!!!

    • Anonymous November 1, 2013 at 2:44 am Reply

      በጣም እንጂ እግዚአብሔር ሁል ግዜ ያስበን ::የ እመቤታችን የቅድስት ድንግል ማርያም አማላጅነት የቅዱሳን የፃድቃን የመላእክት ተራዳይነት አይለየን ::

  3. G.g October 31, 2013 at 5:39 pm Reply

    God Bless You, Fathers.

  4. Abe October 31, 2013 at 10:35 pm Reply

    Really a big step for our Church. Let his spirit be with you all the time!!

  5. WOLET MARIAM October 31, 2013 at 10:43 pm Reply

    Abet Amlake yet agngnche Lamesegeneh!!!! EGZIABEHER YEMESGEN. YABATOCHACHN AMLAK YEMESGEN. AHUNEM YETEBALEWN HULU EWNET YADERGLEN. YEBETEKRSTIANACHNENEM TENSAIE YASAYEN. AMEN!!!!!!!!!!!!!!!!!!!!!!!!!!!!!!!!!!!!!!!!

  6. Anonymous November 1, 2013 at 3:28 am Reply

    እግዚአብሔር አምላክ ሆይ ለአባቶቻችን ብርታትን ለኛም አስተዋይ ልቦናን ስጠን !

  7. Anonymous November 1, 2013 at 6:10 am Reply

    አምላክ የዚህችን ቤተክርስቲያን ችግር አይቶ የምእመኗንም እንባ አብሶ ሊያነሳት እንደሆነ ይሰማኛል!!!

  8. Fassika November 1, 2013 at 11:36 am Reply

    God bless Ethiopia and its people.

  9. Tsione November 1, 2013 at 12:36 pm Reply

    Ayacheu Ewnet tezegyalech enge atetefam. Ahunem YDENGLE MARIAM LEGE MEDHANITACHEN, AMLAKACHEN,GETACHEN, EYESUS KIRSTOS,LEULE EGEZIABHER EWNETUN YAWTALEN. BETECHEMARIAM LEZEH HULU MESEWATENETEN YEMIKEFLUTEN ABATOCHE ENA MAHEBER KIDUSANE ELET ELET EGZIABHERE YETIBEKACHEU. YEMEBETACHEN MILGA, YESADIKAN YESEMAETAT TESLOTEN TERADAIENET AYLEYEN. YEHEZEBUNEM ENBA YEKUTERELEN.

  10. Anonymous November 1, 2013 at 2:39 pm Reply

    yes. the Truth is revealed now. as you know , our True Fathers and brothers had been suffering for a long time to see the result of the truth . praise to the Almighty God, now it is revealed. the enemy of the church and the accuser of our fathers and brothers now under their feet. so, from now on, our beloved church will stand to gather to spread the Gospel throughout the country.
    May God always be on the side of our fathers as well as on our side.

  11. Anonymous November 1, 2013 at 6:37 pm Reply

    ከታህድሶዎች ጋራ ግን በእርቅ መጨረስ የሚለው ነገር አላማረኝም ለምንድነው ከኃይማኖት ጋራ የተያያዘ ጉዳይ በእርቅ የሚያልቀው? መንፈሳዊ ፍርድ ሳይሰጥ የምን እርቅ ነው? ከተቻለ ከቤተክርስቲያን ጠራርጎ ማባረረ እና እዛው የለመዱበት(የሚያሰለጥኗቸው ጋ)መሄድ አለባቸው እንጂ ሌላ ዙር ቤተክርስቲያንን እወካ እንዲመጣ መፈቀድ የለበትም ይህ ምን አልባት በመሰሪ ጳጳሳት ተፈልጎ(ታቅዶ) ሊሆን ይቻላል ምክንያቱም አባቶቻችን የዋሃን ስለሆኑ መሰሪዎቹ ለግዜውም ቢሆን ለማታለል ሊሞክሩ ይችላሉና :: እግዚአብሔር ቤተክርስቲያንን ይጠበቅልን::

  12. Anonymous November 2, 2013 at 3:33 am Reply

    አባቶቻችን ልጆቹን በላይ በላይ ወልዶ በአሁኑ ሰአት በአለው የኑሮ ውድነት የሚንገላተው የቤተክህነት ሰራተኛ እያለ ለሊቃነ ጳጳሳቱ ለእያንዳንዳችሁ 2500 ብር የደመዎዝ ጭማሪ ማድረጋችሁን አስመልክቶ ከጋዜጠኛ የቀረበላችሁን ጥያቄ ሳትመልሱ አደበስብሳችሁ ለምን አለፋችሁት?????

  13. Anonymous November 3, 2013 at 6:55 am Reply

    እጅግ የሚያስገርም ጉዳይ ነው በእውነት በቅርብ በተጠናቀቀው ሲኖዶስ ለጳጳሳቱ ደመዎዝ ጭማሪ አድርጎአል?
    ይህ ተፈጽሞ ከሆነ ጭልጥ ያለ አፍቅሮ ነዋይ ነው ምክንያቱም መነኩሴ ያውም ጳጳስ ለምኑ ነው የገንዘብ ጭማሪ የሚያስፈልገው የነበራቸ ው ደመዎዝ እኮ ከበቂ በላይ ነው የልጆች ማሳደጊያ የወትት የትምህረት ቤት ክፍያ የአልባሳት መግዣ የደብተር የእስኪቢርቶ የእርሳስ መግዣ ያስፈልጋቸዋል አይባል ከዘህ ሁሉ ጣጣ የተለዩ ናቸው በየሀገረስብከታቸው ከደመወዛቸው ሌላ የቤት አስቤዛወቻቸው
    ይሉላቸው አል ለምንድን ነው ያን ያክል ብር ለአንድ ጳጳስ የተከመረው ግልጽ ማብራሪያ ሊሰጥበት ይገባል የገዘቡ ምንጮች ምእመናኑ ናቸው እና፡፡

  14. Anonymous November 3, 2013 at 6:58 am Reply

    እጅግ የሚያስገርም ጉዳይ ነው በእውነት በቅርብ በተጠናቀቀው ሲኖዶስ ለጳጳሳቱ ደመዎዝ ጭማሪ አድርጎአል?
    ይህ ተፈጽሞ ከሆነ ጭልጥ ያለ አፍቅሮ ነዋይ ነው ምክንያቱም መነኩሴ ያውም ጳጳስ ለምኑ ነው የገንዘብ ጭማሪ የሚያስፈልገው
    የነበራቸ ው ደመዎዝ እኮ ከበቂ በላይ ነው የልጆች ማሳደጊያ የወትት የትምህረት ቤት ክፍያ የአልባሳት መግዣ የደብተር የእስኪቢርቶ የእርሳስ መግዣ ያስፈልጋቸዋል አይባል ከዘህ ሁሉ ጣጣ የተለዩ ናቸው በየሀገረስብከታቸው ከደመወዛቸው ሌላ የቤት አስቤዛወቻቸው ይሞሉላቸውአል ለምንድን ነው ያን ያክል ብር ለአንድ ጳጳስ የተከመረው ግልጽ ማብራሪያ ሊሰጥበት ይገባል የገዘቡ ምንጮች ምእመናኑ ናቸው እና፡፡

  15. Anonymous November 7, 2013 at 1:20 pm Reply

    Eny Egziabhern amsgnglhu b/c yttnacre weyyte babatoch ayech alwkemna. So God bless them.

  16. Anonymous November 7, 2013 at 7:36 pm Reply

    men abate alena adise amange hulgizem ashqabach newu menem bogo megbre tefetoale

Leave a comment