የኤጲስ ቆጶሳት አስመራጭ ኮሚቴ ተቋቋመ፤ የዕጩዎችን ዝርዝር ለርክበ ካህናት ምልአተ ጉባኤ ያቀርባል

የቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ በዛሬው፣ ጥቅምት ፳ ቀን ፳፻፮ ዓ.ም ዘጠነኛ ቀን የቀትር በፊት ውሎው የኤጲስ ቆጶሳትን ምርጫ የሚያስፈጽም አስመራጭ ኮሚቴ ሠየመ፡፡

አስመራጭ ኮሚቴው የቅዱስ ሲኖዶስ ዋና ጸሐፊ ብፁዕ አቡነ ሉቃስና ስድስት ሊቃነ ጳጳሳት በአባልነት የሚገኙበት ሲኾን ሊቃነ ጳጳሳቱ የትግራይ፣ ወሎ፣ ጎንደር፣ ጎጃም፣ ሸዋና ኦሮሚያ አህጉረ ስብከትን በመወከል የተመረጡ ናቸው፡፡ በዚህም መሠረት÷ ከትግራይ የልማትና ክርስቲያናዊ ተራድኦ ኮሚሽን ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ሳሙኤል፣ ከወሎ የደቡብ ወሎ ሀ/ስብከት ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ አትናቴዎስ፣ ከጎንደር የሰሜን ጎንደር ሀ/ስብከት ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ኤልሳዕ፣ ከጎጃም የምሥራቅ ጎጃም ሀ/ስብከት ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ማርቆስ፣ ከሸዋ የከምባታ ሐዲያ ጉራጌና ስልጢ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ቀሌምንጦስ እና ከኦሮሚያ የደቡብ ምዕራብ ሸዋ – ወሊሶ ሀ/ስብከት ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ሳዊሮስ በአስመራጭ ኮሚቴ አባልነት ተሠይመዋል፡፡

ዕጩዎችን በሕገ ቤተ ክርስቲያን ለኤጲስ ቆጶሳት ምርጫ በወጣው መስፈርት ብቻና ብቻ ለይቶ እንዲያቀርብ በምልአተ ጉባኤው ከባድ አደራ የተጣለበት አስመራጭ ኮሚቴው÷ ከመስፈርቱ ውጭ ጎጠኝነትን ጨምሮ በተለያዩ መደለያዎች ሢመተ ኤጲስ ቆጶስነትን ለማግኘት ካሰፈሰፉ ቆሞሳት እንዲጠበቅ ከፍተኛ ማስጠንቀቂያ ተሰጥቶታል ተብሏል፡፡

አስመራጭ ኮሚቴው በመምረጫ መስፈርቱ መሠረት የዕጩዎችን ማንነት ከመለየት ባሻገር ከበጀት፣ ከመንበረ ጵጵስና እና ከጽ/ቤቶች መሟላት አኳያ ኤጲስ ቆጶሳቱ ሊመደቡባቸው የሚገቡ አህጉረ ስብከትን በቅደም ተከተል በመለየት ብዛታቸውን የመወሰን ሥራም እንደሚሠራ ተገልጧል፡፡

በጽርሐ መንበረ ፓትርያርክ በሚሰጠው ቢሮ ሥራውን የሚያከናውነው አስመራጭ ኮሚቴው፣ በሥራው ወራት የፍትሕ መንፈሳዊ ድንጋጌ እንደሚያዝዘውና በተሻሻለው የኤጲስ ቆጶሳት ምርጫ ሕግ እንደተመለከተው ተቀባይነት ያለው የግልጽነት መርሕ በመከተልና የልዩ ልዩ ውጫዊ አካላት ጣልቃ ገብነቶችንና ተጽዕኖዎችን በመከላከል አደራውን መወጣት ይኖርበታል፡፡

አስመራጭ ኮሚቴው ሥራውን ጨርሶ ሪፖርቱን የሚያቀርበው ለመጪው የርክበ ካህናት ቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ ሲኾን ሥርዐተ ሢመቱም የምልአተ ጉባኤውን መጠናቀቅ ተከትሎ እንደሚፈጸም ተመልክቷል፡፡

የኤጲስ ቆጶሳትን ምርጫና ተያያዥ ጉዳዮችን የተመለከቱ ሌሎች መረጃዎችን ወደፊት እንደምናቀርብ ከወዲሁ እንገልጻለን፡፡

4 thoughts on “የኤጲስ ቆጶሳት አስመራጭ ኮሚቴ ተቋቋመ፤ የዕጩዎችን ዝርዝር ለርክበ ካህናት ምልአተ ጉባኤ ያቀርባል

  1. dangos October 30, 2013 at 1:32 pm Reply

    may God help them to nominate these fathers they are expected and should be.

  2. Anonymous October 30, 2013 at 1:32 pm Reply

    May God bless our Beloved Fathers. This is very nice decision. The Holy Spirit works with them Indeed.. lets be united and prayer together for our beloved church as well as for our country.

  3. mg November 2, 2013 at 2:52 pm Reply

    This is a good news about our Church.Thanks God, so keep it up,May God bless you, and God bless our country Ethiopian.

  4. Anonymous November 11, 2013 at 4:28 am Reply

    I am sending this message from Newzealand. As you aware, the Holy Synode/ Abune Paulos assigned Melake Tsehai Aba Gebre Selassie Gobena as a General Manager for Australia and Newzealand Hager Sebeket. Unfortunately he left his position since last September 2012 due to his awful things has done here in Melbourne. Now I heard that he is trying to lobby to be a bishop by spending to much money who collected from here. This is to inform to our fathers to do very thoroughly back ground check up for all nominees. If it is possible it is better to contact their respective Hager Sebket or churches.
    May god be with you.
    Girma from Christ Church

Leave a comment