ዐሥራ አራቱን ቅዳሴያት በመስኮብኛ የተረጐሙት ብፁዕ ዶክተር አቡነ ጢሞቴዎስ ዐረፉ

  • ሥርዓተ ቀብራቸው፣ ነገ ረቡዕ ከጸሎተ ቅዳሴ በኋላ በመንበረ ጸባኦት ቅድስት ሥላሴ ካቴድራል ይፈጸማል
  • ወደ ዩኒቨርሲቲ ያደገውን አንጋፋውን የቅድስት ሥላሴ መንፈሳዊ ኮሌጅ፣ ለ20 ዓመታት መርተዋል፤
  • ዐሥራ አራቱን ቅዳሴያት በመስኮብኛ(ሩሲያ ቋንቋ) ተርጉመዋል፤ ስንክሳርን በ800 ገጾች አትተዋል
  • የልማት እና ክርስቲያናዊ ተራድኦ ኮሚሽንን ለ11 ዓመታት በበላይ ሓላፊነት መርተዋል፤

***

የቅድስት ሥላሴ ዩኒቨርስቲ እና የመንበረ ጸባዖት ቅድስት ሥላሴ ካቴድራል የበላይ ጠባቂ ብፁዕ ዶክተር አቡነ ጢሞቴዎስ ዐረፉ፡፡

የ83 ዓመት የዕድሜ ባለጸጋ የኾኑት አረጋዊው ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ጢሞቴዎስ፣ ትላንት መጋቢት 27 ቀን 2013 ዓ.ም. ሌሊት፣ ከዚኽ ዓለም ድካም ማረፋቸውን፣ የቅዱስ ሲኖዶስ ዋና ጸሐፊ እና የሐዋሳ እና ጌዴኦ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ዮሴፍ በሰጡት መግለጫ አስታውቀዋል፡፡

የብፁዕ አቡነ ጢሞቴዎስ ዜና ዕረፍት እንደተሰማ፣ የቋሚ ሲኖዶስ አባላት እና በቅርብ ያሉ ብፁዓን አባቶች፣ ዛሬ ጠዋት በቅዱስ ፓትርያርኩ መሪነት መወያየታቸውንና የብፁዕነታቸውን ሽኝት እና የቀብር ሥነ ሥርዓት አስመልክቶ ውሳኔዎችን ማሳለፋቸውን ብፁዕ ዋና ጸሐፊው ገልጸዋል፡፡

በዚኽም መሠረት፣ ዛሬ ማክሰኞ ከቀኑ በ11፡00፣ ቅዱሳን ፓትርያርኮች፣ ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት፣ የጠቅላይ ቤተ ክህነት ጽ/ቤት እና የዐዲስ አበባ ሀገረ ስብከት ሓላፊዎች እና ሠራተኞች እንዲሁም የዐዲስ አበባ ሀገረ ስብከት ገዳማት እና አድባራት አስተዳዳሪዎች በተገኙበት፣ በመንበረ ጸባኦት ቅድስት ሥላሴ ካቴድራል ለብፁዕነታቸው ጸሎት ይደረጋል፡፡

ከዚኹ ጋራ ተያይዞ፣ ነገ ረቡዕ፣ መጋቢት 29 ቀን 2013 ዓ.ም. ከረፋዱ በ4፡00 ጸሎተ ፍትሐት ይደረጋል፤ ጸሎተ ቅዳሴውም እንዳበቃ የቀብር ሥነ ሥርዓታቸው ለረጅም ጊዜ ባገለገሉበት በዚያው በመንበረ ጸባኦት ቅድስት ሥላሴ ካቴድራል ይፈጸማል፡፡

በመኾኑም፣ ቅዱሳን ፓትርያርኮች እና ብፁዓን አባቶች በተገኙበት ነገ ከቀትር በኋላ በሚፈጸመው የብፁዕነታቸው የቀብር ሥነ ሥርዓት፣ ካህናት እና ምእመናን እንዲሁም የብፁዕነታቸው የመንፈስ ቅዱስ ልጆቻቸው እና ወዳጆች፣ በካቴድራሉ ተገኝተው ሽኝት እንዲያደርጉላቸው ብፁዕ ዋና ጸሐፊው ጥሪ አስተላለፈዋል፡፡

#################

የብፁዕ አቡነ ጢሞቴዎስ ዜና ሕይወት እና ሥራዎች በአጭሩ

ብፁዕ አቡነ ጢሞቴዎስ፣ ከአባታቸው ከባላምባራስ ተስፋ ተኰላ እና ከእናታቸው ከወይዘሮ ካህሳ(ወለተ ዮሐንስ) ኃይሉ፣ በቀድሞ አጠራር በትግራይ ክፍለ ሀገር በዓድዋ አውራጃ በብዘት ወረዳ በፊልፈሎ መድኃኔዓለም ቀበሌ በ1930 ዓ.ም. ተወለዱ፡፡

ዕድሜአቸው ለትምህርት እንደ ደረሰ፣ የቤተ ክርስቲያንን መሠረተ ትምህርት በመድኃኔዓለም ቤተ ክርስቲያን ከአጎታቸው ከመልአከ ሰላም ገብረ አረጋዊ ተማሩ፡፡ ትምህርታቸው ለማስፋፋት ወደ አኵስም ተጉዘው ሐለማት ከሚባለው ቦታ እና በአቡነ ጰንጠሌዎን ገዳም ከመምህር ገብረ ዮሐንስ፣ ለሙሉ ዲቁና የሚያበቃቸውን ትምህርት ከተማሩ በኋላ በ1942 ዓ.ም. ወደ አሥመራ ሔደው፣ የኤርትራ ሊቀ ጳጳስ ከነበሩት ከብፁዕ አቡነ ማርቆስ ማዕርገ ዲቁና ተቀበሉ፡፡

ወደተወለዱበት ብዘት ወረዳ ተመልሰው ለጥቂት ዓመታት በፊልፈሎ መድኃኔዓለም ቤተ ክርስቲያን በዲቁና እንዳገለገሉ፣ በዓድዋ አውራጃ በዓዲ አርባዕተ ወረዳ ወደሚገኘው ደብረ ሃሌ ሉያ አቡነ ሳሙኤል ገዳም ገብተው፣ ጸዋትወ ዜማን ከመሪጌታ ይትባረክ፣ መዝገብ ቅዳሴን ከመምህር ገብረ እግዚአብሔር ተምረዋል፤ ከትምህርታቸው ጋራም በረድእነት በኋላም በመጋቢነት እያገለገሉ ሥርዓተ ምንኵስናን በ15 ዓመታቸው በዚኹ ገዳም ፈጽመዋል፤ ኃይለ ሥላሴ ይባል የነበረው ዓለማዊ ስማቸውም አባ ሀብተ ሥላሴ በሚል ተተካ፡፡ በኋላም ማዕርገ ቅስናን ከኤርትራ ክፍለ ሀገር ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ማርቆስ ተቀብለዋል፡፡

ብፁዕ አቡነ ጢሞቴዎስ፣ በትምህርት ላይ እያሉ የአቡነ ሳሙኤል ገዳም የንብረት አስተዳደር ሓላፊ በመኾን፥ የዕቃ ግምጃ ቤት፣ የእህል ጐተራ እና የውኃ ማጠራቀሚያ ገንዳዎችን አሠርተዋል፡፡ በገዳሙ አካባቢ ይኖሩ የነበሩት ሴቶች፣ የወንዶች ገዳም በኾነው በአቡነ ሳሙኤል ገዳም መገልገል ባለመቻላቸው ችግራቸውን ተገንዝበው ሌሎች ረዳቶችን ይዘው በራሳቸው ጉልበት በገዳሙ አጠገብ የቅድስት ማርያም ቤተ ክርስቲያንን ሠርተው ለሴቶች አገልግሎት እንዲውል አድርገዋል፡፡

ከደብረ ሃሌ ሉያ የዓመታት ትምህርት እና ከፍተኛ አገልግሎት በኋላ የዘመናዊ ትምህርት ፍለጋ በ1950 ዓ.ም. ወደ አዲስ አበባ መጡ፡፡ በዐዲስ አበባ እያሉ ጠቅላይ ቤተ ክህነቱ ወደ ትምህርት ቤት እንዲያስገባቸው ደጅ በመጥናት ላይ እያሉ፣ በቤተ ክህነቱ አዳሪ ት/ቤት ገብቶ ለመማር መስፈርቱ የቅኔ ችሎታ መኾኑን በመረዳታቸው ወደ ጎጃም አቅንተው በእነማይ ወረዳ በምትገኘው መንግሥቶ ኪዳነ ምሕረት ከመምህር ደጉ ቅኔን አጥንተዋል፡፡ በ1950 ዓ.ም. ወደ ዐዲስ አበባ ተመልሰው፣ በመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተ ክህነት ተቋቁሞ በነበረው የፈታኝ ኮሚቴ ከሌሎች ጋራ ተወዳድረው በከፍተኛ ውጤት በማለፋቸው፣ ሐረር ወደሚገኘው የራስ መኰንን የመምህራን ማሠልጠኛ መንፈሳዊ ትምህርት ቤት ተልከው በአዳሪነት በመግባት የአንደኛ ደረጃ ትምህርታቸውን በሦስት ዓመታት ውስጥ አጠናቀዋል፡፡

መደበኛ አገልግሎታቸውን በሐረር ጻድቁ አቡነ ተክለ ሃይማኖት ቤተ ክርስቲያን በማድረግ፣ በየክብረ በዓላቱ በሌሎችም አብያተ ክርስቲያንም እያገለገሉ የስምንተኛ ክፍል ብሔራዊ ፈተናን አልፈው፣ ወደ ዐዲስ አበባ በመመለስ፣ በቅድስት ሥላሴ መንፈሳዊ ኮሌጅ በመግባት የኹለተኛ ደረጃ ትምህርታቸውን አጠናቀዋል፡፡ ትምህርታቸውን እየተከታተሉ፣ በመንበረ ጸባኦት ቅድስት ሥላሴ ካቴድራል አገልግለዋል፤ በመንፈሳዊ ኮሌጅ ወጣቶች ይካሔድ በነበረው የስብከተ ወንጌል አገልግሎት በብዙ ተሳትፈዋል፡፡

ከዚህ በኋላ የሩስያ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን ለኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በሰጠችው የነፃ ትምህርት ዕድል መሠረት፣ ከአራት ቀሳውስት እና ዲያቆናት ጋራ በጠቅላይ ቤተ ክህነት ወደ ሶቭየት ኅብረት ለከፍተኛ ትምህርት ተላኩ፡፡ በሌኒንግራድ አካዳሚ ለአራት ዓመታት የሚሰጠውን ትምህርት ከተከታሉ በኋላ፣ ዐሥራ አራቱን ቅዳሴያት ወደ ሩሲያ ቋንቋ በመተርጐም በከፍተኛ ውጤት በማጠናቀቃቸው፣ ለዶክትሬት ትምህርት እንዲቀጥሉ የነበሩበት የትምህርት ተቋም ዕድል ሰጣቸው፡፡ በዚህ መሠረት ለዶክትሬት ማዕርግ የሚያበቃቸውን ትምህርት ለአራት ዓመታት ተከታትለው፣ ስለ ቤተ ክርስቲያን ታሪክንና ስለ ስንክሳር በሩሲያ ቋንቁ 800 ገጽ ጽፈው ለአካዳሚው አቅርበው ጽሑፋቸው ተቀባይነት በማግኘቱ በዶክትሬት ማዕረግ ተመርቀዋል፡፡

ብፁዕ አቡነ ጢሞቴዎስ ከሶቭየት ኅብረት ከተመለሱ በኋላ፣ የቅዱስ ጳውሎስ ከፍተኛ መንፈሳዊ ት/ቤት ዳይሬክተር በመኾን ነበር ሥራቸውን የጀመሩት፡፡ ከዚያም በኋላ፣ የመንበረ ጸባኦት ቅድስት ሥላሴ ካቴድራል ሊቀ ሥልጣናት ኾነው ተሹመዋል፡፡ የመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተ ክህነት የውጭ ግንኙነት መምሪያ ሓላፊ እና የገዳማት መምሪያ ሓላፊ ኾነው አገልግለዋል፤ ቤተ ክርስቲያንን በዐበይት የዓለም አብያተ ክርስቲያናት ጉባኤያት በመወከል ተሳትፈዋል፡፡

በፊት ስማቸው ቆሞስ ዶክተር አባ ሀብተ ሥላሴ ተስፋ ይባሉ የነበሩት ብፁዕነታቸው፣ በሦስተኛው ፓትርያርክ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ተክለ ሃይማኖት አንብሮተ እድ ጥር 4 ቀን 1972 ዓ.ም. ማዕርገ ጵጵስና ከተሾሙት ሦስት አባቶች አንዱ የነበሩ ሲኾን፣ ብፁዕ አቡነ ጢሞቴዎስ ተብለው፣ በከፋ ክፍለ ሀገር የጊሚራ እና የማጂ አውራጃ ሀገረ ስብከት ኤጲስ ቆጶስነት ተመድበዋል፡፡ ከዚህ በኋላ የልማት እና ክርስቲያናዊ ተራድኦ ኮሚሽን ሊቀ ጳጳስ ኾነው በመሥራት ላይ እያሉ ከቅዱስነታቸው ጋራ በተፈጠረ አለመግባባት ከልማት ኮሚሽን ተነሥተው በጂማ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስነት ተመድበው ለሰባት ዓመታት በቆዩበት ጊዜ፣ 11 አብያተ ክርስቲያንን ያሠሩ ሲኾን፣ በዘመን ብዛት የተጎዱ 31 ሕንፃ አብያተ ክርስቲያንን አሳድሰዋል፡፡ ለቤተ ክርስቲያን የገቢ ምንጭ ለመፍጠር፣ ዘጠኝ ፕሮጀክቶችን አዘጋጅተው፥ መጋዝን፣ ልዩ ልዩ የጐጆ ኢንዱስትሪዎች፣ ሦስት የዕንጨት መሰንጠቂያ ማሽኖችንና የእህል ወፍጮዎችን ተክለዋል፡፡ ከጅማ ከተማ ውጪ 30ሺሕ ካሬ ሜትር የእርሻ መሬት ከመንግሥት አስፈቅደው አትክልት፣ ፍራፍሬ እና ልዩ ልዩ የምግብ ሰብሎችን አምርተዋል፡፡ ዛሬም በልማት ሐዋርያው ብፁዕ አቡነ እስጢፋኖስ የሚመራው ሀገረ ስብከቱ፣ ብፁዕ አቡነ ጢሞቴዎስ የጀመሯቸውን የልማት ሥራዎች በማጠናከር ከእርሻ መሬቱ በማልማት ተጠቃሚ በመኾን ላይ ይገኛል፡፡

ከብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ተክለ ሃይማኖት ዕረፍት በኋላ የልማት እና ክርስቲያናዊ ተራድኦ ኮሚሽን እንቅስቃሴ በመዳከሙ፣ ራብዓይ ፓትርያርክ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ መርቆሬዎስ ብፁዕነታቸውን ወደ ቀድሞ ሓላፊነታቸው መለሷቸው፡፡ በዚህ ወቅት በሰሜኑ የሀገራችን ክፍል በመንግሥት እና በተቃዋሚ ኃይሎች መካከል የነበረው ጦርነት ተፋፍሞ ሰለነበረ፣ በመቶ ሺሕዎች ለስደት እና መፈናቀል ተዳርገው በአስከፊ ችግር ላይ ነበሩ፡፡ በወቅቱ ተከሥቶ የነበረው ድርቅም የሕዝቡን ችግር አባብሶት ነበር፡፡ በመኾኑም ብፁዕነታቸው፣ ከኢትዮጵያ ካቶሊካዊት፣ ወንጌላዊት እና ከመካነ ኢየሱስ ተወካዮች ጋራ በመኾን፣ በአውሮጳ፣ በልዩ ልዩ አሜሪካ ግዛቶች እና በካናዳ በመዘዋወር ለተቸገረው ሕዝብ የነፍስ አድን ርዳታ በመጠየቅ፣ በጥሬ ገንዘብ እና በዓይነት በርካታ ርዳታ አስገኝተዋል፡፡ ይህም ሰብአዊ ረድኤት ከየቦታው የተፈናቀለውን ሕዝብም ሕይወት ለማዳን ችሏል፡፡

በ1983 ዓ.ም. የሥርዓተ መንግሥት ለውጥ ወቅት በእርስ በርስ ጦርነቱ የተፈናቀለውን ሕዝብ ለማቋቋም እና የአገራችንን የመልሶ ግንባታ ጥረት ለመደገፍ፣ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ልማት እና ክርስቲያናዊ ተራድኦ ኮሚሽን፣ በብፁዕ አቡነ ጢሞቴዎስ አባታዊ አመራር ከፍተኛ ሚና ተጫውቷል፡፡

የገጠር መንገዶችን በመሥራት፣ ለገበሬዎች የእርሻ በሬ እና የወተት ላሞችን በማደል፣ ምርጥ ዘር ለገበሬው በማሠራጨት፣ ት/ቤቶችን፣ ክሊኒኮችን፣ የጤና ኬላዎችን በመሥራት፣ የእህል ወፍጮ በመትከል፣ የንጹሕ ውኃ አገልግሎት በገጠር በማስፋፋት ለኅብረተሰቡ ከፍተኛ አገልግሎት አበርክቷል፡፡ ከተፈጥሮ ደን የተራቆተውን መሬቱ እንዲያገግም የዛፍ ችግኞችን በማፍላት እና ለገበሬዎች በማደል፣ የዛፍ ችግኞችን በማስተከል፣ መሬት እንዲያገግም ከሰው እና ከእንስሳት ንክኪ ነጻ እንዲኾን በማድረግ፣ የዕርከን ሥራዎችን በማከናወን ኮሚሽኑ ከፍተኛ አስተዋፅኦ አድርጓል፡፡ አትክልት እና ፍራፍሬ በማልማት እና ስላጠቃቀሙ ተግባራዊ ሥልጠና በመስጠት የገጠሩን ሕዝብ ሕይወት ለመለወጥ በተደረገው ጥረት፣ ኮሚሽኑ በብፁዕነታቸው አመራር ከፍተኛ አስተዋፅኦ አበርክቷል፡፡ እያንዳንዱ ሀገረ ስብከትም የገቢ ምንጭ ለመፍጠር ያካሒድ ለነበረው የገጠር ልማት ሥራ፣ በሐሳብ እና በገንዘብ ረድተዋል፡፡ ገዳማት የራስ አገዝ ልማት ሥራዎችን እንዲያካሒዱ በማገዝ በችግር እንዳይዘጉ እና መነኰሳትም እንዳይሰደዱ ከፍተኛ ድጋፍ ሰጥተዋል፡፡ በየአህጉረ ስብከቱም የካህናት ማሰልጠኛ ማዕከላትን በማቋቋም፣ ካህናትን በስብከተ ወንጌል እና በገጠር ልማት ሥራ አሠልጥነዋል፡፡ እያንዳንዱ ሀገረ ስብከትም በሥልጠናው ተጠቃሚ ኾኗል፡፡

ብፁዕ አቡነ ጢሞቴዎስ፣ ለዐሥራ አንድ ዓመት ካገለገሉበት ከልማት እና ክርስቲያናዊ ተራድኦ ኮሚሽን ተነሥተው ለኹለት ዐሥርት ዓመታት ወዳገለገሉበት አንጋፋው የቅድስት ሥላሴ መንፈሳዊ ኮሌጅ የበላይ ሓላፊ ሊቀ ጳጳስ ኾነው የተመደቡት በ1991 ዓ.ም. ነበር፡፡ መንፈሳዊ ኮሌጁ ከነበረው የመደበኛ ትምህርት በተጨማሪ የማታ ትምህርት መርሐ ግብር በመክፈት፣ አከታትሎም የርቀት ትምህርት እና ከ2008 ዓ.ም. ጀምሮ የአዲስ አበባ ካህናት በአማርኛ ልዩ ትምህርት እንዲያገኙ ዐዲስ የትምህርት ፕሮግራም አስከፍተዋል፡፡ ከ2005 ዓ.ም. ጀምሮ ደግሞ የኹለት ዓመት የድኅረ ምረቃ የትምህርት ፕሮግራም አስጀምረዋል፡፡ የመንፈሳዊ ኮሌጁ የትምህርት ፕሮግራም በመስፋፋቱ የሚያስፈልገውን ወጪ ለመሸፈን፣ ባለአራት ፎቅ ሕንፃ በ2000 ዓ.ም. በ58 ሚሊዮን ብር አስገንብተዋል፡፡ ወደ ዩኒቨርሲቲ ለማሳደግ በነበረው ዕቅድም፣ የማስተማሪያ እና ልዩ ልዩ የትምህርት መገልገያ ክፍሎች ያሉት ባለአራት ፎቅ ኹለገብ ሕንፃ በ133 ሚሊዮን ብር አስገንብተው አስመርቀዋል፡፡

ብፁዕ አቡነ ጢሞቴዎስ ከመደበኛ ሓላፊነታቸው በተጨማሪ በልዩ ልዩ የቤተ ክርስቲያን ተቋማት እየተመደቡ አገልግለዋል፡፡ የሰበታ ቤተ ደናግል ጠባባት የሴቶች ገዳን በመርዳት፣ የምስካየ ኅዙናን ገዳም የቦርድ አባል በመኾን፣ የሕፃናት እና ቤተሰብ ጉዳይ ድርጅት የቦርድ ሰብሳቢ በመኾን አገልግለዋል፡፡ ብፁዕነታቸው አሁን ያላቸው ምኞት የተጀመረውን የኮሌጁን ሕንፃ አጠናቀው ዩኒቨርሲቲ ለመክፈት፣ ለዩኒቨርስቲው የሚመጥን የሰው ኃይል በማደራጀት እንዲሁም ለትምህርት የሚተጉ፣ በሥነምግባር የታነጹና ቤተ ክርስቲያን ፍጹም ታማኝ አገልጋዮችንና መሪዎችን ማስተማርና ማሰልጠን ነው፡፡ ከዚያም በኋላ፣ በልማት እና ክርስቲያናዊ ተራድኦ ኮሚሽንና በመጨረሻም ከ1992 ዓ.ም. እስከ ጥቅምት 2011 ዓ.ም.፣ የቅድስት ሥላሴ መንፈሳዊ ኮሌጅ የበላይ ሓላፊ ሊቀ ጳጳስ ኾነው ሰፊ አባታዊ አገልግሎት አበርክተዋል፡፡

ብፁዕ አቡነ ጢሞቴዎስ፣ በአንጋፋው የቅድስት ሥላሴ መንፈሳዊ ኮሌጅ፣ ለኻያ ዓመታት ያኽል የነበራቸው የበላይ ሓላፊነት ቆይታ፣ በበርካታ ክሦች እና ውዝግቦች የተመላውን ያኽል፣ መንፈሳዊ ኮሌጁ ወደ ዩኒቨርሲቲ ደረጃ ለተሸጋገረበት ተቋማዊ ዕድገት እና መስፋፋት የነበራቸው አስተዋፅኦ ተጠቃሽ ነው፡፡ ከአምስተኛው ፓትርያርክ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ጳውሎስ ጋራም የነበራቸውን ቅርበት ያኽል፣ ከሌሎች አባቶች ጋራ ከሓላፊነት እስከ መታገድ የደረሱበት እና “መርሐ ተዋሕዶ” የተሰኘ ጋዜጣ በማቋቋም ይፋ የወጣ ውዝግብ፣ በመጨረሻም በመንግሥት አካል ተሳትፎ ጭምር በተቋቋመው አጣሪ ኮሚሽን፣ መሠረታዊ አስተዳደራዊ ችግሮች የተፈተሹበትና ለሕገ ቤተ ክርስቲያን የ1991 ዓ.ም. ማሻሻያ አንድ ምክንያት የኾኑበት፣ አጋጣሚ ብፁዕነታቸው የሚታወሱበት ነው፡፡

ቤተ ክርስቲያን የበዓለ ጥምቀት ማክበሪያ ቦታዎቿን ለማልማት ዕቅድ መንደፏን አስታወቀች

  • በአ/አበባ ሀ/ስብከት በስሟ የሚገኙ 38 ይዞታዎችን ያቀፈ ዕቅድ ነው፤
  • የሌሎች 40 ማክበሪያዎችን ይዞታ ለማረጋገጥ ምላሽ እየጠበቀች ነው፤
  • የጃንሜዳ ባሕረ ጥምቀት ባለቤትነቷን የሚያረጋግጥ ካርታ ጠይቃለች
  • ከዕሴቷ ጋራ የማይቃረኑ የልማት ፕሮጀክቶችን ለመተግበር ዐቅዳለች፡፡

***

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን፣ ጃንሜዳን ጨምሮ በአዲስ አበባ የሚገኙ የበዓለ ጥምቀት ማክበሪያ ቦታዎችን ለማልማት ዕቅድ የነደፈች ሲኾን፣ የጃንሜዳ ባለቤትነቷን የሚያረጋግጥ  ካርታ እንዲሰጣት ጠይቃለች፡፡

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያንን የካርታ እና የይዞታ ጉዳይን የሚከታተለው እና በአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ መልከ ጸዴቅ የሚመራው ኮሚቴ፣ ሰሞኑን  ከአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ጋራ ባደረገው ውይይት፣ ቤተ ክርስቲያን በስሟ የሚገኙ 38 የባሕረ ጥምቀት ቦታዎችን በተለያየ መልኩ የማልማት ዕቅድ እንዳላት ማስታወቁን፣ የአዲስ አበባ ሰንበት ት/ቤቶች አንድነት የመረጃ ክፍል ሓላፊ ላዕከ ሰላም ግርማ ተክሉ ለአዲስ አድማስ ተናግረዋል፡፡

አብዛኛዎቹ የበዓለ ጥምቀት ማክበሪያዎች፣ በመንግሥትም በግል ባለሀብቶችም እየተቀነሱ በመወሰድ ላይ እንዳሉና ይኸውም ቦታዎቹ፣ በዓመት አንድ ጊዜ ብቻ ለጥምቀት በዓል ማክበሪያነት አገልግለው ከዚያ በኋላ ሳይሠራባቸው መክረማቸውን በመመልከት እንደኾነ የሚጠቅሱት ላዕከ ሰላም ግርማ፣ ይህ ኹኔታ ያሳሰባት ቤተ ክርስቲያን፣ ቦታዎቹን የማልማት  ዕቅድ መንደፏን ገልጸዋል፡፡

በተለይ ቤተ ክርስቲያኒቱ በአዲስ አበባ ከተማ ከሚገኙት 78 ጠቅላላ የበዓለ ጥምቀት ማክበሪያዎች ውስጥ፣ የይዞታ ማረጋገጫ ካርታ በተረከበችባቸው 38ቱ የጥምቀት ማክበሪያ ቦታዎች ላይ፣ ከእምነቱ ዕሴት ጋራ የማይቃረኑ የማኅበራዊ ልማት ፕሮጀክቶችን ለመተግበር መታቀዱን ነው ላዕከ ሰላም ግርማ ያስረዱት፡፡ በተቀሩትም ቦታዎች የይዞታ ማረጋገጫ ካርታ እንደተገኘባቸው ወደ ልማት እንዲገቡ አቅጣጫ መቀመጡን አመልክተዋል፡፡

በቦታዎቹ ላይ ሊተገበሩ ከታቀዱት የማኅበራዊ ልማት ፕሮጀክቶች መካከል፥ ቤተ መጻሕፍት፣ የመናፈሻ ውስጥ ክፍት የማንበቢያ ቦታዎች፣ ከሥርዓተ እምነቱ ጋራ የማይቃረኑ የመዝናኛ እና የመናፈሻ አገልግሎት መስጫዎች እና አረንጓዴ ልማት የማከናወን ዕቅዶች እንደሚገኙበት ሓላፊው አብራርተዋል፡፡

የቦታዎቹ ሃይማኖታዊ ክብር ተጠብቆ ማኅበራዊ ግልጋሎትን በሰፊው እንዲሰጡ ዕቅድ መነደፉን፣ ይህም፣ ከአረንጓዴ ልማት አቅጣጫ ጋራ የተስማማ የአረጋውያን፣ የወጣቶች እና የልዩ ልዩብረተሰብ ክፍሎች የመንፈስ ማደሻ ቦታዎች እንዲኾኑ ያደርጋል፤ በዚኽም ቋሚ እና ጊዜያዊ የሥራ ዕድሎችን ለማስገኘት ምቹ ኹኔታ ይፈጥራል፤ የቦታዎቹንም ቅርስነት ጠብቆ ለማቆየት ያስችላል፤ ያሉት ላዕከ ሰላም ግርማ፣ በዚኽ ረገድ ከውጭ አገር ተመሳሳይ የዐደባባይ የሃይማኖት በዓላት ማክበሪያ ሥፍራዎች አጠባበቅ ልምድ መወሰዱን ገልጸዋል፡፡

በአኹኑ ወቅት በስፖርት ኮሚሽን ባለቤትነት ሥር የሚገኘውና በዓለ ጥምቀት በብሔራዊ ደረጃ የሚከበርበት ታሪካዊው የጃንሜዳ ባሕረ ጥምቀት፣ የጥምቀት በዓል በዩኔስኮ ዓለም አቀፍ የማይዳሰስ ቅርስ ኾኖ ሲመዘገብ፣ በዋናነት የተጠቀሰ የበዓሉ ማክበሪያ ቦታ እንደመኾኑ፣ ቤተ ክርስቲያን ባለቤትነቷን የሚያረጋግጥ ካርታ እንዲሰጣት ጥያቄ አቅርባ ምላሽ እየጠበቀች እንደምትገኝ ጠቁመዋል፤ ምላሹ እንደተገኘም፣ ቦታውን በተለያየ መልኩ ለማልማት ቤተ ክርስቲያን ዕቅድ መንደፏን ለአዲስ አድማስ አስረድተዋል፡፡

የጃንሜዳ ባለቤትነት ለቤተ ክርስቲያን ቢደረግም፣ ወትሮ የነበረውን የስፖርት  ማዘውተሪያነት ከሌሎች የማኅበራዊ ልማት ሥራዎች ጋራ አቀናጅቶ እንዲሰጥ ይደረጋል፤ ተብሏል፡፡ (አዲስ አድማስ፤ ጥር ፩ ቀን ፳፻፲፫ ዓ.ም.) 

በሌላ በኩል፣ በአዲስ አበባ ከተማ ከሚገኙ 78 የበዓለ ጥምቀት ማክበሪያዎች ውስጥ 40ዎቹ፥ ለአረንጓዴ ልማት(ግሪን ኤሪያ) በሚል በተያዙ፣ የስፖርት ኮሚሽን የይዞታ ካርታ ባወጣባቸው፣ በግለሰብ አርሶ አደሮች ይዞታዎች፣ በዐደባባዮች መሀል ላይ እና በጋዝ ማደያዎች ውስጥ እንደሚገኙ ተመልክቷል፡፡ ከእኒህም ውስጥ፣ የበዓለ ጥምቀት ማክበሪያነታቸው  በሕጋዊ ካርታ እንዲረጋገጥ ላለፉት 14 ዓመታት ሲጠይቁ ቢቆዩም፣ ምላሽ ያልተሰጣቸው አድባራት እንዳሉ ተጠቁሟል፡፡ ጉዳዩን አስመልክቶ፣ ጴጥሮሳውያን የቤተ ክርስቲያን ክብር እና መብት አስጠባቂ ኅብረት፣ በሳምንቱ መጀመሪያ ላይ፣ ከምክትል ከንቲባ ወ/ሮ አዳነች አቤቤ እና በምክትል ከንቲባ ማዕርግ የአገልግሎት ሰጪ ተቋማት አስተባባሪ አቶ ዣን ጥራር ዓባይ ጋራ ተወያይቷል፡፡

የኅብረቱ ተወካዮች፣ ችግሩንና መፍትሔ ለመስጠት የሚያስችሉ አማራጮችን በዝርዝር ያስረዱ ሲኾን፣ ማሻሻያ ያስፈልጋቸዋል የተባሉ መመሪያዎችንም አንሥተዋል፡፡ ምክትል ከንቲባዋም፣ በተጠቀሱት የበዓለ ጥምቀት ማክበሪያ ቦታዎች የሚገኙ አድባራት፣ ለአኹኑ በዓሉን የሚያከብሩበት መንገድ በጊዜያዊነት እንዲመቻችና ከበዓሉ በኋላ በኹለት ሳምንታት ጊዜ ውስጥ ከሚመለከታቸው ባለሞያዎች ጋራ ጉዳዩን መርምረው ኹነኛ እልባት እንደሚሰጡ ለተወካዮቹ አስታውቀዋል፡፡ በመኾኑም፣ የዘንድሮውን በዓለ ጥምቀት ከሌሎች አድባራት ጋራ ተደርበው ለማክበር የሚችሉበት ኹኔታ፣ ከየአድባራቱ ሓላፊዎች ጋራ በመመካከር መመቻቸቱ ተገልጿል፡፡

የከተማ አስተዳደሩ የጃንሜዳን ባሕረ ጥምቀት ይዞታ ለቤተ ክርስቲያን ለማረጋገጥ ትኩረት እንዲሰጥ ቅዱስ ፓትርያርኩ ጠየቁ

  • ጃንሜዳን ለበዓለ ጥምቀት ዝግጁ የማድረግ ሥራ በይፋ ተጀምሯል

ጃንሜዳን ለበዓለ ጥምቀት ዝግጁ የማድረግ ሥራ፣ ዛሬ ኀሙስ፣ ታኅሣሥ 8 ቀን 2013 ዓ.ም. ማለዳ 12:00 ሰዓት ላይ፣ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአኵስም ወእጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት፣ ብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት፣ ክብርት ምክትል ከንቲባ አዳነች አቤቤ እና የከተማ አስተዳዳደሩ ከፍተኛ የሥራ ሓላፊዎች በተገኙበት በይፋ ተጀምሯል።

ቅዱስ ፓትርያርኩ በክንውኑ ላይ ባስተላለፉት አባታዊ መልእክት፣ የከተማ አስተዳደሩ የጥምቀት በዓል ከመድረሱ በፊት ጃንሜዳን አጽድቶ ለማስረከብ በገባው ቃል መሠረት የገበያ መዋያውን በማንሣት እና በማጽዳት፣ ለበዓሉ ዝግጁ በማድረጉ የተሰማቸውን ደስታ ገልጸዋል። የይዞታ ባለቤትነቱን በማረጋገጥ ረገድም፣ የከተማ አስተዳደሩ ትኩረት እንዲሰጥበት ጠይቀዋል።

ክብርት ምክትል ከንቲባ አዳነች አቤቤ በበኩላቸው፣ የኮረና ቫይረስ ወረርሽኝን ተከትሎ የከተማዋን ሕዝብ ከቫይረሱ ሥርጭት ለመታደግ ሲባል፣ የአትክልት ገበያው ወደ ጃንሜዳ መዘዋወሩ እና እስከ ዛሬ ድረስ አገልግሎት እየሰጠ መቆየቱን ጠቅሰው፣ የከተማ አስተዳደሩ ከጥምቀት በዓል አንድ ወር በፊት የአትክልት ገበያውን ከጃንሜዳ ሙሉ በሙሉ በማንሣት ቦታውን ለበዓሉ ዝግጁ የማድረግ ሥራ በማከናወን ላይ እንደሚገኝ ተናግረዋል።

ምክትል ከንቲባዋ አያይዘውም፣ በቀሪዎቹ ቀናት መሬቱን የመደልደል እና አረንጓዴ የማድረግ ሥራ፣ በከተማ አስተዳደሩ በኩል ተጠናከሮ እንደሚቀጥል አመልክተው፣ በቤተ ክርስቲያኒቱ የተደራጁ ወጣቶችም የከተማ አስተዳዳሩ ከሚያከናውነው ሥራ ጎን በመቆም የበኩላቸውን አስተዋፅኦ እንደሚያበረክቱ እምነታቸው ገልጸዋል። በቀጣይም፣ በጃንሜዳ ባለቤትነት በሚነሡ ጉዳዮች ዙሪያ፣ ከቤተ ክርስቲያኒቱ ጋራ በመመካከር እና በመወያየት እንደሚሠሩ ተናግረዋል።

አትክልት ተራ፣ በአኹኑ ሰዓት ከጃንሜዳ ባሕረ ጥምቀት ሙሉ በሙሉ መነሣቱ ተረጋግጧል።

ምንጭ፦ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ሕዝብ ግንኙነት መምሪያ

የዓለም ኹሉ ቅርስ የኾነው በዓለ ጥምቀት የማንም ቅርስ እንዳይኾን የማድረግ ዘመቻ!?

  • በዓሉ እንዳይከበር ከማስታጎል ጀምሮ የማክበሪያ ቦታዎችን መንጠቅ እየተለመደ መጥቷል፤
  • ከአዲስ አባባ 78 የበዓሉ ማክበሪያዎች፣ ይዞታቸው በሕግ የተረጋገጠላቸው 38ቱ ብቻ ናቸው፤
  • ለቀሪዎቹ 40 ማክበሪያዎች ካርታ እንዲሰጣት ቤተ ክርስቲያን ብትጠይቅም ምላሽ አላገኘችም፤
  • በያዝነው ዓመት ብቻ፣ በልዩ ልዩ ክፍላተ ከተማ ከ6 በላይ የማክበሪያ ይዞታዎች ተነጥቀዋል
  • ከ40 በላይ ገዳማት እና አድባራት የዘንድሮውን በዓለ ጥምቀት የሚያከብሩበት ቦታ የላቸውም
  • በልማት እና በስፖርት ማዘውተሪያ ሰበብ፣ መንጠቅ እና ምትክ አለመስጠት ተባብሶ ቀጥሏል

***

  • በማስተር ፕላኑ ታሳቢ ሳይደረጉ መንገድ የወጣባቸውና ጠፍ የኾኑ አብሕርተ ምጥምቃት አሉ፤
  • መንግሥት ዝንፈቱን በጊዜ አርሞ ካላስተካከለ፣ የቅርሱን ደረጃ እና ህልውና አስጊ ያደርገዋል፤
  • የቱሪስት መስሕብ የኾነውን ሳይጠብቁ ተመራጭ እና ቀዳሚ መዳረሻ መኾን እንደምን ይቻላል?
  • ክብርት ም/ል ከንቲባዋ፣የጃንሜዳን ጽዳት በማስጀመር ላሳዩት ቁርጠኝነት ምስጋና እናቀርባለን
  • ጃንሜዳን ጨምሮ የኹሉም ባሕረ ጥምቀት ይዞታዎቻችን ባለቤትነት በሕጋዊ ካርታ ይረጋገጥ
  • ይዞታዎቹን መዳፈር የዓለም ቅርስ በዓለ ጥምቀት የማንም ቅርስ እንዳይኾን ማድረግ ነው!

***

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በዐደባባይ ከምታከብራቸው ዐበይት በዓላት አንዱ፣ የጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ጥምቀት በዓል ነው። በየዓመቱ ጥር 10 ቀን ታቦታት ከመንበረ ክብራቸው ወጥተው፣ በካህናት ሃሌታ እና በምእመናን እልልታ ታጅበው ወደ ባሕረ ጥምቀት ወርደው በጊዜያዊነት በዚያው ዓርፈው፣ ደማቅ እና ማራኪ ሃይማኖታዊ ሥነ ሥርዓት የሚፈጸምበት፣ ልዩ እና ተናፋቂ ማኅበራዊ መስተጋብሮች የሚከናወኑበት ጥንታዊ እና ታሪካዊ በዓል ነው – በዓለ ጥምቀት፡፡

ከ1500 ዓመታት በላይ ሳይቋረጥ የተከበረው እና በመከበር ላይ ያለው፣ በአገራዊ ዕሴትነቱ እና የውጪ ጉብኝዎችን በመሳብ ወደር የማይገኝለት ሕብራዊው የጥምቀት – ከተራ ሥነ በዓል፣ የኢትዮጵያውያንና የመላው ዓለም የማይዳሰስ ቅርስ በመኾን፣ በ2011 ዓ.ም. በተባበሩት መንግሥታት የትምህርት የሳይንስ እና የባህል ድርጅት፣ የሰው ልጆች ኹሉ መንፈሳዊ ሀብት ኾኖ ተመዝግቧል።

የጥምቀት በዓል፣ ለበዓሉ ማክበርያነት ተብሎ በፈለገ ዮርዳኖስ አምሳል በተከተረው ባሕረ ጥምቀት ዙሪያ መከበር የሚገባው ሲኾን፣ በቱሪስት መስብሕነቱ በምጣኔ ሀብቱ ዘርፍ ለሀገር የጎላ አስተዋፅኦ የሚያበረክት ሃይማኖታዊ፣ ታሪካዊ እና ሀገራዊ ዕሴት እና ቅርስ ነው፡፡ ይኹን እንጂ ከቅርብ ጊዜያት ወዲህ፣ ይህ ታላቅ የዐደባባይ በዓላችን፣ ከባሕረ ጥምቀት ይዞታ እና ዝግጅት ጋራ በተያያዘ ዕንቅፋት እየገጠመው ነው፡፡ ይህም፣ የጥምቀትን ሥነ በዓል ከነሙሉ መንፈሱ እና ክብሩ ጠብቆ ለትውልድ ለማዝለቅ አዳጋች እያደረገው መጥቷል።

በዓለ ጥምቀት፣ በዩኔስኮ የማይዳሰስ ዓለም አቀፍ ቅርስ ኾኖ ከተመዘገበ በኋላ፣ ለአከባበሩ ድምቀት ድርሻ ያላቸው አካላት፣ ካለፈው በተሻለ ሚናቸውን እየተወጡ ጥበቃ እና ክብካቤ ያደርጋሉ ተብሎ ነበር የተጠበቀው። በተፃራሪው፣ በዓሉ እንዳይከበር ከማስተጓጎል ጀምሮ የጥምቀት ማክበሪያ ቦታዎችን እስከ መንጠቅ የደረሰ ድፍረት እየተለመደ መጥቷል። በክልል ከተሞች፣ ዞኖች፣ ወረዳዎች፣ ቀበሌዎች፣ ጎጦች እና በአዲስ አበባ ከተማ ጭምር፣ በመንግሥት መዋቅር ውስጥ ያሉ አንዳንድ ባለሥልጣናት ሳይቀሩ፣ የማስተጓጎል ድርጊቱ አባሪ እና ተባባሪ እየኾኑ ይገኛሉ።

በዚኽ ረገድ፣ በአገራችን የጥምቀት በዓል በብሔራዊ ደረጃ የሚከበርበት የጃንሜዳ ባሕረ ጥምቀት፣ በይዞታ ባለቤትነት ያለበትን ችግር በአስረጅነት መጥቀስ ይቻላል፡፡ በዓለ ጥምቀትን በዩኔስኮ የዓለም ቅርስነት ለማስመዝገብ የአከባበር ናሙና ከተወሰደባቸው ቦታዎች ውስጥ አንዱ ነው – ጃንሜዳ።  ከ11 በላይ ታቦታት ማደሪያ የኾነው የጃንሜዳ ባሕረ ጥምቀት፣ በዓሉ በታላቅ ድምቀት የሚከበርበት፣ ልዩ ልዩ ኢትዮጵያዊ የባህል ዕሴቶች ተሰናስነው የሚገለጡበት ታሪካዊ ቦታ ነው። ይኹንና፣ ቀደም ሲል የተረጋገጠው የቤተ ክርስቲያናችን የባለቤትነት ካርታ ተነጥቆ ለሌላ አካል ተላልፎ ተሰጥቷል፡፡ ይልቁንም፣ ገጽታውን የሚያጠፋ የገበያ መዋያ ኾኖ ክብሩን ሲያጣና የሚመለከተው መንግሥታዊ አካል ለጉዳዩ የሰጠውን አነስተኛ ግምት ስንመለከት፣ “በእጅ ያለ ወርቅ እንደ መዳብ ይቆጠራል” ያሰኛል። በተለይ፣ የአዲስ አበባ ባህል እና ቱሪዝም ቢሮ እንዲሁም የባህል እና ቱሪዝም ሚኒስቴር፣ የበዓሉን ማክበሪያ ቦታዎች ከማስጠበቅ ጀምሮ፣ በዓለም አቀፍ ቅርሱ ቀጣይ አያያዝ እና ክብካቤ ዙሪያ የሚጠበቅባቸውን ሓላፊነት በባለቤትነት መንፈስ ሲወጡ አይስተዋሉም። ሌሎች መንግሥታዊ አካላትም፣ በዓሉ እና የበዓሉ ማክበሪያ ቦታዎች ያላቸውን ሃይማኖታዊ ትስስር እና ክብር በውል ከመረዳት አኳያ ባለባቸው ውስንነት፣ ይዞታዎቹን እንዲዳፈሩና በዓሉ በሚገባው መጠን እንዳይከበር ምክንያት ኾነዋል፡፡

የባህል እና ቱሪዝም ሚኒስቴር፣ ኢትዮጵያን ከአምስት የአፍሪቃ ተመራጭ እና ቀዳሚ የቱሪስት መዳረሻዎች አንዱ ማድረግን ዋና ዓላማው አድርጎ እየሠራ እንደሚገኝ ገልጿል። ኾኖም፣ ለቱሪስት ፍሰት መስሕብ ለኾነው ቦታ እና ትዕይንት መጠበቅ ትኩረት ሳይሰጡ፣ የመዳረሻነት ግብን እንደምን በቀጣይነት ማሳካት ይቻላል? ጥምቀትን የመሳሰሉ የዐደባባይ በዓላት የማክበሪያ ቦታዎች ይዞታ በየሰበቡ እየተሸራረፈ እና እየተቀማ የሥነ በዓሉ ቀጣይነት አጠያያቂ ሲኾን፣ ቅርሶች ያሉበትን ተጨባጭ ኹኔታ በማጥናት እና በመገምገም የመጠበቅ፣ የመከባከብ እና ቀጣይ የማድረግ ግዴታ ያለበት ሚኒስቴሩ፣ እንደ ባለድርሻ አካል ድምፁን የሚያሰማው መቼ ይኾን? ቅርሶቹ በፈተና ውስጥ ውድቀው ከጠፉ በኋላ ወይም በመዘገባቸው አካል የመሰረዝ ዕጣ ፈንታ ሲገጥማቸው ነውን? ስለ ጃንሜዳ እና ጥምቀት በዓል አከባበር ምንም አለማለቱ እና በበዛ ዝምታ ውስጥ መሰንበቱ ለምን ይኾን?

በአዲስ አባባ ከተማ ከሚገኙት 78 የጥምቀት በዓል ማክበሪያ ቦታዎች(የታቦታት ማደሪያዎች) መሀከል፣ በሕጋዊ ካርታ የተረጋገጠ ማስረጃ ያላቸው 38 ብቻ ሲኾኑ፣ ቀሪዎቹ 40 የማክበሪያ ቦታዎች፣ ካርታ እንዲሰጣቸው ቤተ ክርስቲያን ለከተማ አስተዳደሩ ጥያቄ አቅርባ እስከ አሁን ምላሽ አላገኘችም፡፡ አብዛኞቹ የይዞታ ማረጋገጫ ካርታ ያልተሰጣቸው የጥምቀት በዓል ማክበሪያ ቦታዎች፣ በቤተ ክርስቲያን ለዘመናት ተይዘው መንፈሳዊ አገልግሎት ሲሰጥባቸው የኖሩ ናቸው፤ ቀሪዎቹም የዓመታት የአገልግሎት ዕድሜ የሚቆጠርላቸውና እስከ ዛሬም እየተገለገለችባቸው የሚገኙ ናቸው።

ከቅርብ ጊዜ ወዲህ፣ አንዳንድ የመንግሥት ተቋማት እና ልዩ ልዩ አካላት በሚያሳዩት የማናለብኝነት መንፈስ፣ ገሚሶቹ ተነጥቀዋል፤ ቀሪዎቹም አደጋ ተጋርጦባቸዋል። በተለይ ባለፉት ኹለት ዓመታት፣ ቤተ ክርስቲያንን ስትገለገልባቸው የነበሩ ይዞታዎቿ፣ በጠራራ ፀሐይ እየተነጠቁ ለግንባታ እና ሌላ ዓላማ እየዋሉ ይገኛሉ፡፡ በያዝነው ዓመት ብቻ፣ በርእሰ መዲናዪቱ የተለያዩ ክፍላተ ከተማ፣ ከስድስት በላይ የባሕረ ጥምቀት ይዞታዎች በመነጠቃቸው፣ ከ40 በላይ ገዳማት እና አድባራት የዘንድሮውን በዓለ ጥምቀት የሚያከብሩበት ቦታ የላቸውም። ከወዲሁ አፋጣኝ መፍትሔ የማይሰጥ ከኾነም፣ መጪውን የጥምቀት በዓል የማያከብሩ አድባራት እና ገዳማት እንደሚኖሩ አያጠራጥርም።

በሌላ በኩል፣ ከአዲስ አበባ ከተማ መቆርቆር አስቀድሞ እና የማስተር ፕላን ጥናት ከመጀመሩ በፊት እንዲሁም ከከተማው ማስተር ፕላን ትግበራ በፊት አገልግሎት ሲሰጡ የቆዩና ረጅም ዘመን ያስቆጠሩ የባሕረ ጥምቀት ይዞታዎች እንዳሉ ይታወቃል። በከተማዋ መመሥረት እና መስፋፋት ሒደት ግን፣ ለዘመናት የሚታወቁበት አገልግሎታቸው በማስተር ፕላኑ ታሳቢ ሳይደረግ፣ መንገድ የወጣባቸው እና ጠፍ የኾኑ አብሕርተ ምጥምቃት አሉ። በከተማዋ ማስፋፋት እና በልማት ስም በተለይ በስፖርት ማዘውተሪያነት ሰበብ የታቦት ማደሪያዎችን መንጠቅ እና ምትክ አለመስጠት ተባብሶ ቀጥሏል።

የጥምቀት በዓል በዩኔስኮ ዓለም አቀፍ የማይዳሰስ ቅርስ መመዝገቡን ታሳቢ በማድረግ፣ የከተማ አስተዳደሩ አስቀድሞ የይዞታ ማረጋገጫ ካርታ የሰጣቸው የጥምቀት በዓል ማክበሪያ ቦታዎች እንዳሉ ቢታወቅም፣ በባሕረ ጥምቀት የይዞታ ካርታዎች ላይ ደርቦ ለሌላ አካል ተጨማሪ ካርታ መሰጠቱ ቤተ ክርስቲያንን በእጅጉ አሳዝኗል፡፡ ይህ ተግባር፣ የሥራ አፈጻጸም ክፍተት ብቻ ኾኖ ሊታይ አይችልም፡፡ ይልቁንም፣ የመላው ዓለም መስሕብ እና መንፈሳዊ ቅርስ የኾነውን በዓል፣ የሀገር ዕሴት እንኳን ኾኖ እንዳይቀጥል ከማጥፋት ተለይቶ የማይታይ ነው፡፡ በመኾኑም፣ የጉዳዩ አያያዝ ወዴት እያመራ እንዳለ በጥልቀት እንድንመረምር አስገድዶናል።

በአዲስ አበባ ሰንበት ት/ቤቶች አንድነት እምነት፣ በጥቂት ሹማምንት እና አበሮቻቸው ጥቅመኝነት እና ጽንፈኝነት በመነጨ ማናለብኝነት እየተከሠተ ያለው ይህ ዓይነቱ አሠራር፣ ለአገራችን ሰላም እና ልማት ቀጥተኛ አደጋ የሚጋርጥ ነው፡፡ መንግሥት ዝንፈቱን በጊዜ አርሞ እስካላስተካከለው ድረስ፥ የአምልኮ ነፃነትን የሚፃረር እና የኦርቶዶክሳውያንን ትዕግሥት የሚፈታተን ብሎም የዓለም አቀፉን መንፈሳዊ ቅርስ ደረጃ በሒደት ጥያቄ ውስጥ የሚያስገባ እንዳይኾን አስቸኳይ እልባት እንዲሰጠው እንጠይቃለን፡፡ በዋና ከተማዪቱ እና በሌሎችም ክልሎች፣ በጥንታዊቷ እና ታሪካዊቷ ቤተ ክርስቲያን ላይ እየተፈጸመ የሚገኝ መዳፈር በመኾኑ፣ አንድነቱ ፈጽሞ እንደማይታገሠው ለማሳሰብ እንወዳለን።  

በዚህ አጋጣሚ፣ የአዲስ አባባ ከተማ አስተዳደር፣ ቀደም ሲል የጥምቀት ማክበሪያ ይዞታዎችን በካርታ አረጋግጦ ለመስጠት የሔደበትን ርቀት እናደንቃለን፡፡ አኹንም ታሪካዊውን ጃንሜዳን ጨምሮ ጥያቄ ለቀረበባቸው ሌሎችም ቦታዎች፣ ከመጪው የጥምቀት በዓል በፊት ምላሽ እና መፍትሔ በመስጠት፣ ሀገር ለኾነችው እናት ቤተ ክርስቲያን ያለውን ክብር እና ለዓለም አቀፉ የሰው ልጆች መንፈሳዊ ሀብት መጠበቅ ተቆርቋሪነቱን በተግባር በማሳየት ግዴታውን እንደሚወጣ ተስፋ እናደርጋለን።

በመጨረሻም፣ የአዲስ አበባ ከተማ ምክትል ከንቲባ ክብርት ወ/ሮ አዳነች አበቤ፣ የጃንሜዳን ባሕረ ጥምቀት ክብር በማይመጥንና ከቤተ ክርስቲያን ዕውቅና ውጪ ለአትክልት ሽያጭ ሥራ የዋለበት ኹኔታ እንዲስተካከል ላሳዩት ትጋት ምስጋናችንን እንገልጻለን፡፡ በአንድ ሳምንት ውስጥ የአትክልት መሸጫዎቹ ፈርሰው እና ተወግደው ለበዓሉ ዝግጁ እንዲኾን መመሪያ በመስጠት እና የጃንሜዳን ጽዳት በማስጀመር ወደ ቀደመ ክብሩ ለመመለስ ምክትል ከንቲባዋ ያሳዩት ቁርጠኝነት፣ የጥምቀት በዓል እንደቀደሙት ጊዜያት ኹሉ በዓይነተኛ ይዘቱ እና ገጽታው ለማክበር፣ ዓለም አቀፋዊ ቅርስ የኾነበት ደረጃው እና ድምቀቱ ተጠብቆ ለትውልድ ለማሰተላለፍ የሚያስችል ሓላፊነትን የመወጣት ጅማሮ ነውና ቢዘገይም የሚያስመሰግን ተግባር ነው።

በቀጣይም፣ የበዓሉን ቀን መቃረብ ታሳቢ በማድረግ፣ ቦታው ለቅድመ ዝግጅት ሥራዎች እንዲመቻች ያደርጉልን ዘንድ ጥያቄአችንን እናቀርባለን፡፡ በራሱ ታሪክ የኾነውን ጃንሜዳን ጨምሮ የይዞታ ማረጋገጫ ካርታ ጥያቄ የቀረበባቸውን የባሕረ ጥምቀት ይዞታዎች እንዲሁም አላግባብ በመነጠቃቸው ሳቢያ የበዓል ማክበሪያ ቦታ ለሌላቸው ገዳማት እና አድባራት ከበዓሉ በፊት ምትክ በመስጠት እና በሕጋዊ ካርታ በማረጋገጥ ይዞታቸውን የማጽናት ታሪካዊ ሥራ እንዲሠሩ፣ በመላ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ሰንበት ትምህርት ቤቶች ስም በታላቅ አክብሮት እንጠይቃለን።

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን

የሰንበት ትምህርት ቤቶች አንድነት

አዲስ አበባ

ታኅሣሥ 3 ቀን 2013 ዓ.ም.

ብፁዕ ዶክተር አቡነ ገብርኤል ዐረፉ

• “የማውቀውን እናገራለኹበሚል ርእስ የሰዱት ግለ ታሪካቸው ለስርጭት ተዘጋጅቷል

• በነገረ መለኰት የማስተርስ እና የፒኤችዲ ዲግሪዎች የሞስኮ እና የፕሪስተን ምሩቅ ነበሩ፤

ሥርዓተ ቀብራቸው፣ ነገ እሑድ በመንበረ ጸባኦት ቅድስት ሥላሴ ካቴድራል ይፈጸማል

***

የሲዳማ ጌዲዮ እና ቡርጂ ዞኖች አህጉረ ስብከትን በሊቀ ጳጳስነት ያገለገሉት ብፁዕ ዶክተር አቡነ ገብርኤል ዓረፉ፡፡

ብፁዕነታቸው፣ ባለፈው ጥቅምት ቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ መደበኛ ስብሰባ፣ ከእርግና እና ሕመም ጋራ በተያያዘ ከሓላፊነታቸው ተገልለው ረዳት እንዲመድብላቸው መወሰኑ የሚታወስ ሲኾን፣ ዛሬ ቀትር ገደማ በመንበረ ፓትርያርኩ መኖሪያቸው በተወለዱ በ80 ዓመት ዕድሜአቸው ዓርፈዋል፡፡

የብፁዕነታቸው የሽኝት እና የቀብር ሥነ ሥርዓት በቋሚ ሲኖዶስ የሚወሰን ሲኾን፣ ነገ እሑድ ሰንበት፣ ኅዳር 27 ቀን 2013 ዓ.ም. ከቅዳሴ ውጪ፣ በመንበረ ጸባኦት ቅድስት ሥላሴ ካቴድራል እንደሚፈጸም ተጠቁሟል፡፡

ከካህን አባታቸው ከመምህር ገብረ ሕይወት እና ከእናታቸው ከወ/ሮ ብርነሽ፣ በወሎ ክፍለ ሀገር በዋግ አውራጃ በ1933 ዓ.ም. የተወለዱት ብፁዕነታቸው፣ የወሎ ክፍለ ሀገር ሊቀ ጳጳስ ከነበሩት ብፁዕ አቡነ ይሥሓቅ ማዕርገ ዲቁናን፤ በደብረ ሊባኖስ ገዳም ከቆሞስ ሊቀ ምርፋቅ ኤርሚያስ ሥርዓተ ምንኵስናን በ1958 ዓ.ም.፤ ሥልጣነ ቅስናን ከወለጋ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ያዕቆብ በ1959 ዓ.ም. ተቀብለዋል፡፡

የቅኔንና የአገባብን ይትበሃል በሚገባ አጠናቀው በመምህርነት የተመረቁት፣ የአቋቋም እና የትርጓሜ መጻሕፍት ዐዋቂው ብፁዕ አቡነ ገብርኤል፣ በ1962 ዓ.ም. ወደ ቀድሞዋ ሶቭየት ኅብረት ተልከው ከሌኒን ግራድ መንፈሳዊ ኮሌጅ የማስተር ኦቭ ዲቪኒቲ ዲግሪያቸውን በከፍተኛ ውጤት አግኝተዋል፡፡

የዶክትሬት ዲግሪያቸውን በዚኹ መንፈሳዊ ኮሌጅ ቀጥለውና በሚገባ ፈጽመው በትምህርተ ሥጋዌ(ክሪስቶሎጂ) ዶክትሬታቸውን ተቀብለዋል፡፡ ወደ ሰሜን አሜሪካ ዘልቀውም፣ ከፕሪስተን ዩኒቨርሲቲ የማስተር ኦቭ ቴዎሎጂ ዲግሪ በመጨመር የነገረ መለኰት ዕውቀታቸውን በከፍተኛ ደረጃ አጠናክረዋል፡፡ የዶክትሬት ሥራቸው፥ ሞስኮ እና ኒውዮርክ በሚገኙት የዩኔስኮ የትምህርት ኮሚሽኖች ተመርምሮ ጸድቆላቸዋል፡፡

ትምህርተ ሃይማኖት ቁጥር 1 እና ቁጥር 2 እንዲሁም ክብረ ቅዱሳን ከተሰኙት መጻሕፍት በተጨማሪ፣ በጋዜጠኞቹ መ/ር ጌታቸው በቀለ እና መ/ር ተስፋዬ ሽብሩ አማካይነት ለረጅም ጊዜ ሲሰንዱ የቆዩት ግለ ታሪካቸው፣ የማውቀውን እናገራለኹ በሚል ርእስ ተዘጋጅቶ እና የኅትመት ሒደቱ ተጠናቅቆ ለሥርጭት በዝግጅት ላይ ይገኛል፡፡

በአገልግሎት ረገድም፣ በዐዲስ አበባ የገነተ ጽጌ ቅዱስ ጊዮርጊስ ካቴድራል ሰባኬ ወንጌል እና የእሑድ ት/ቤት መምህር ኾነው ለስድስት ዓመታት አገልግለዋል፡፡ በደብረ ገሊላ ቅዱስ ዐማኑኤል ካቴድራል እና በሰዋስወ ብርሃን ቅዱስ ጳውሎስ ት/ቤት፣ ለኮርሰኛ ካህናት በክረምት ወራት ትምህርት ሰጥተዋል፡፡ በአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት የማኅደረ ስብሐት ቅድስት ልደታ ለማርያም ካቴድራል፣ የሠርክ ጉባኤን በቀዳሚነት ወጥነው አስፋፍተዋል፡፡

የመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተ ክህነት የትምህርት እና ማሠልጠኛ መምሪያ ሓላፊ ኾነው ተመድበው፣ በልዩ ልዩ አህጉረ ስብከት የካህናት ማሠልጠኛዎች እንዲከፈቱ ከፍተኛ ጥረት አድርገዋል፡፡ የልማት እና ክርስቲያናዊ ተራድኦ ኮሚሽን ዋና ጸሐፊ ኾነው በመሾም፣ በልዩ ልዩ ገዳማት የልማት ሥራዎችን አከናውነዋል፡፡ በጠቅላይ ቤተ ክህነት ጽ/ቤት የመንፈሳዊ አገልግሎት መምሪያ መጋቤ ካህናት ኾነው ተሹመው ከፍተኛ አገልግሎት አበርክተዋል፡፡

ብፁዕ ዶ/ር አቡነ ገብርኤል፣ በፊት ስማቸው ዶ/ር አባ ኢያሱ(ጴጥሮስ) ገብሬ ይባሉ የነበረ ሲኾን፤ ጥር 4 ቀን 1972 ዓ.ም. በሦስተኛው ፓትርያርክ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ተክለ ሃይማኖት አንብሮተ እድ ከተሾሙት ሦስት ኤጲስ ቆጶሳት አንዱ ነበሩ፡፡ በሢመተ ጵጵስናው፣ የቅድስት ሥላሴ መንፈሳዊ ኮሌጅ ኤጲስ ቆጶስ በመኾን ነበር ሓዋርያዊ አገልግሎታቸውን የጀመሩት፡፡ በኋላም በኤርትራ፣ በድሬዳዋ፣ በደቡብ ሸዋ፣ በምዕራብ ሸዋ፣ በቅድስት ሀገር ኢየሩሳሌም፣ በሰሜን አሜሪካ ሐዋርያዊ አገልግሎታቸውን ቀጥለው በመጨረሻም፣ የሲዳማ ቡርጂ እና ጌዲዮ ዞኖች አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ በመኾን አባታዊ ተልዕኳቸውን በትጋት ፈጽመው በዛሬው ዕለት ከዚኽ ዓለም ድካም ዓርፈዋል፡፡

የብፁዕ አባታችን የድካማቸው በረከት ይድረሰን፡፡

ለአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት ዋና ሥራ አስኪያጅነት እና ዋና ጸሐፊነት የውድድር ማስታወቂያ ወጣ

  • በተለይ በሥራ አመራር ወይም በሰው ሀብት አስተዳደርየመጀመሪያ ዲግሪዎችን ይጠይቃል፤
  • በአስተዳደር እና በፋይናንስ የሥራ መስኮች ቢያንስ የ5 ዓመታት የሥራ ልምድ ያስፈልጋል፤
  • ለዋና ሥራ አስኪያጅነት የሚወዳደሩ፥የአመራር ሐሳባቸውን በጽሑፍ መግለጽ ይጠበቅባቸዋል፤

***

  • የሃይማኖት ሕጸጽ የሌለባቸው፣ ጎጠኝነትን የሚጠየፉና በሙስና የማይጠረጠሩ ይወዳደሩ
  • አመልካቾች እስከ ኅዳር 21 ቀን ድረስ በቢሮ ቁጥር 303 ማስረጃቸውን ማቅረብ አለባቸው፤
  • ብቁ አገልጋይ በመሾም የሥራውን መንገድ አስተካክሎ ለመጀመር የወጣ ማስታወቂያ ነው

***

የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት እንደ ሌሎቹ አህጉረ ስብከት ኹሉ ራሱን ችሎ በሊቀ ጳጳስ እንዲመራ በቅዱስ ሲኖዶስ መወሰኑን ተከትሎ፣ ለጽ/ቤቱ ዋና ሥራ አስኪያጅ እና ዋና ጸሐፊ በውድድር ለመመደብ ሀገረ ስብከቱ ማስታወቂያ አወጣ፡፡

የውድድሩ ዓላማ፣ ለቦታው የሚመጥን ብቁ አገልጋይ በማግኘት እና በመሾም የሥራውን መንገድ አስተካክሎ ለመጀመር እንዲቻል መኾኑን በማስታወቂያው ያስገነዘበው የሀገረ ስብከቱ ጽ/ቤት፣ መስፈርቶቹን የሚያሟሉ አመልካቾች በውድድሩ እንዲሳተፉ አስታውቋል፡፡

በትምህርት ዝግጅት ረገድ አመልካቾች፣ ከአብነት ትምህርቶች ቢያንስ በአንዱ ምስክር ያላቸው፣ በነገረ መለኰት እና በዘመናዊው የማኅበራዊ ሳይንስ መስክ በተለይም በአስተዳደር፣ በሥራ አመራር ወይም በሰው ሀብት አመራር የመጀመሪያ ዲግሪ ሊኖራቸው እንደሚገባ በማስታወቂያው ተገልጿል፡፡ የሥራ ልምድን በተመለከተ፣ በአዲስ አበባ ገዳማት እና አድባራት በአስተዳደር እና በፋይናንስ መስኮች ለአምስት ዓመት እና ከዚያ በላይ መሥራትን እንደሚጠይቅ ተመልክቷል፡፡

ለዋና ሥራ አስኪያጅነት የሚወዳደሩ አመልካቾች፣ ሀገረ ስብከቱን እንደምን ለመምራት እንደሚፈልጉ ከሦስት ገጽ ባላነሰ እና ባልበለጠ ጽሑፍ ዐሳባቸውን ማቅረብ የሚጠበቅባቸው ሲኾን፣ ለሚመደቡበት ሓላፊነት በሚፈለገው ኹኔታ በራሳቸው ፕሮጀክት ቀርጸው የማቅረብ እንዲሁም የግጭት አፈታት ስልትን በመጠቀም ችግሮችን ፈትቶ የማስተካከል ችሎታ እና ልምድ ሊኖራቸው እንደሚገባ ተጠቅሷል፡፡

ሥልጣነ ክህነት ያላቸው እና በክህነታዊ አገልግሎትም(በቅዳሴ፣ በማሕሌት፣ በሰዓታት እና በስብከተ ወንጌል) በበቂ ኹኔታ ማገልገል ይጠበቅባቸዋል፡፡ የሃይማኖት ሕጸጽ የሌለባቸው፣ በክርስቲያናዊ ሥነ ምግባራቸው፥ ጎሠኝነትንና ጎጠኝነትን የሚጠየፉ፣ በሙስና የማይጠረጠሩ፣ በአድመኝነትና በአሳዳሚነት የማይታወቁ፣ በወንጀል ጉዳይ ተከሠው በፍርድ ቤት ያልተወሰነባቸው መኾን ይኖርባቸዋል፡፡

የተዘረዘሩትን መስፈርቶች የሚያሟሉ አመልካቾች፣ ከዛሬ ኅዳር 16 እስከ ኅዳር 21 ቀን 2013 ዓ.ም. ድረስ ማስረጃዎቻቸውን፣ በቢሮ ቁጥር 303 በአካል በመቅረብ እንዲያመለክቱ የሀገረ ስብከቱ ጽ/ቤት አስታውቋል፡፡ በሕገ ቤተ ክርስቲያን አንቀጽ 53 ንኡስ አንቀጽ 8 መሠረት፣ የሀገረ ስብከቱ ሊቀ ጳጳስ፣ በትምህርት ችሎታው እና በሥራ ልምዱ ብቁ የኾነ ሰው መርጠው ለብፁዕ ጠቅላይ ሥራ አስኪያጁ በማቅረብ እንዲሾም እንደሚያደርጉ የተደነገገ ሲኾን፣ ዕጩዎችን የመምረጫ መሳፍርትም በዚኹ ድንጋጌ ከፊደል ተ.ቁ(ሀ) እስከ (መ) በዝርዝር ሰፍረዋል፡፡

የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከትን አጠቃላይ የአሠራር ሥርዓት ገምግሞ በማስተካከል ላይ የሚገኘው የብፁዕ አቡነ መልከ ጼዴቅ አስተዳደር፣ የጽ/ቤቱን ጊዜ አላግባብ የሚሻማውንና ለብልሽት የዳረገውን የአጥቢያ አብያተ ክርስቲያን ዐዲስ የሥራ ቅጥር፣ ዕድገት፣ ዝውውር ፈላጊዎች እና የደመወዝ ጭማሬ ጥያቄ ዎችን ጨምሮ ላልተወሰነ ጊዜ እንደማያስተናግድ ቀደም ሲል አስታውቋል፡፡

በምትኩ፣ የጽ/ቤቱን አመራር ከወዲሁ አስተካክሎ ተፈላጊውን ተቋማዊ ማሻሻያ ለማምጣት፣ ለከፍተኛ ምደባዎች(ሹመቶች) መስፈርት አዘጋጅቶ በዚኽ መልኩ የውድድር ማስታወቂያ በማውጣት የጀመረው ግልጽ እና ለተጠያቂነት የሚያመች አካሔድ፣ በሌሎችም አሠራሮች ሊበረታታ እና ሊጠናከር የሚገባው ነው፡፡ በመኾኑም፣ በሞያቸው አስተዋፅኦ ለማድረግ የሚፈቅዱ እና የሚችሉ የቤተ ክርስቲያን ልጆች ኹሉ በተግባር በመሳተፍ ሊደግፏቸው እና ሊያግዟቸው ይገባል፡፡

በብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርካችን ስም መነገድ ይቁም! ከጥቅመኞች፣ ከሥልጣን ጥመኞች እና ከልዩ ተልእኮ አራማጆች ቤተ ክርስቲያናችንን እንጠብቃለን!

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ በጥቅምቱ የመጀመሪያ ዓመታዊ መደበኛ ስብሰባ ያሳለፈውን ውሳኔ አስመልክቶ ከሰንበት ትምህርት ቤቶች አንድነት የተሰጠ ወቅታዊ መግለጫ

++++++++++++++++

የቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ፣ ከጥቅምት 11 እስከ 23 ቀን 2013 ዓ.ም. ባካሔደው የመጀመሪያ ዓመታዊ መደበኛ ስብሰባው በአጀንዳነት ይዞ እንዲመለከታቸው፣ ሀገር አቀፉ የሰንበት ትምህርት ቤቶች አንድነት ጉባኤ በአቀረባቸው ዐበይት ወቅታዊ ጥያቄዎች ዙሪያ ተወያይቶ ተፈላጊውን ውሳኔ መስጠቱ ይታወቃል፡፡

ለሰንበት ት/ቤቶች ግንባር ቀደም ተሳትፎ አጽንዖት በመስጠት የተላለፈው ይኸው የቅዱስ ሲኖዶስ ውሳኔ እና መመሪያ፣ ቤተ ክርስቲያናችን እየደረሰባት ያለውን ውጫዊ ተጽዕኖ እና ጥቃት በመቋቋም እና በመከላከል ጠንክራ ለመውጣት የሚያስችላት ከመኾኑም በላይ፣ ተጋላጭ ያደረጋትን የውስጣዊ አሠራር ክፍተት በመቅረፍ ሐዋርያዊ ተልእኮዋን በአግባቡ ለመፈጸም የሚያበቃት በመኾኑ፣ የልጅነት ጥያቄአችንን ተቀብለው ተገቢውን ምላሽ ለሰጡን ለብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርካችንና ለብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት ያለንን ልባዊ ምስጋና እና አክብሮት አስቀድመን እናቀርባለን፡፡

ከሰንበት ት/ቤቶች አንድነት ጥያቄዎች መካከል አንዱ፣ የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከትን አስተዳደራዊ ጉዳዮች የተመለከተ ነበር። በሀገረ ስብከቱ በሰው ሀብት አስተዳደር በኩል የሚታየው አድሏዊነት፣ ጎጠኝነት፣ የሥራ ዋስትና ማጣት እና እንግልት፤ በፋይናንስ አሠራር እና በንብረት አያያዝ ረገድ የተንሰራፋው የሀብት ብክነት እና ምዝበራ በመባባሱ፣ በተለዋዋጭ ጥቅመኞች በየጊዜው መወረሩ በአገልጋዮች ላይ ያስከተለው የሥነ ምግባር ዕጦት እና በምእመናን ላይ ያሳደረው የመንፈስ ዝለት ከቁጥጥር ውጭ ወጥቶ ጠቅላላ ውድቀት ከመድረሱ በፊት መገታት ይኖርበታል፡፡

ይህ አሳፋሪ እና አሳዛኝ ኹኔታ ሊገታ የሚችለው ደግሞ፣ ቀደም ሲል በብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአኵስም ወዕጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት መመሪያ ሰጪነት ተዘጋጅቶ እና በቅዱስ ሲኖዶስ ጸድቆ እንዲተገበር የተወሰነው የመዋቅር፣ አደረጃጀት እና አሠራር ለውጥ ሲተገበር ነው፡፡ የለውጥ ትግበራ ቅድመ ዝግጅቱ፣ በ2006 ዓ.ም. ተጀምሮ የነበረ ቢኾንም፣ ሕገ ወጥ ጥቅማቸውን በሚያቋርጥባቸው አማሳኞች አድማ ሒደቱ እንዲሰናከል ተደርጓል፡፡ በመኾኑም፣  የሰንበት ት/ቤት አንድነት፣ በአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት ግልጽነት እና ተጠያቂነት ያለውን አሠራር በማስፈን ኹለንተናዊ መፍትሔ ለመስጠት የሚያስችለው ጥናታዊ ለውጥ በቁርጠኝነት እንዲተገበር ምልዓተ ጉባኤውን በአጽንዖት ጠይቆ ነበር።

የቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤም፣ ጥያቄያችንን፥ “ሕገ ቤተ ክርስቲያንን ስለማሻሻል” በሚል በያዘው አጀንዳ ውስጥ አካቶ እና በጥያቄያችን ላይ ተመሥርቶ፣ የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከትን የብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርክ ልዩ ሀገረ ስብከት የሚያደርገውን የሕጉን አንቀጽ 50 ንኡስ አንቀጽ(1) ድንጋጌ መርምሯል፡፡

በዚሁ ምርመራውም፣ ሀገረ ስብከቱ በአሁኑ ወቅት ካለው የሰው ኃይል ክምችት፣ የገንዘብ እና የንብረት ሀብት አንጻር፣ ተጠያቂነትን የሚያረጋግጥ የቅርብ አመራር እና ክትትል እንደሚያስፈልገው ታሳቢ በማድረግ፤ አበ ብዙኃን የኾኑት ቅዱስ ፓትርያርኩ የቤተ ክርስቲያኒቱ ርእስ እንደመኾናቸው አጠቃላይ አመራር የመስጠት ሓላፊነት እንዳለባቸው በመገንዘብ፤ የልዩ ሀገረ ስብከት ድንጋጌው በአፈጻጸሙ፥ ለአድሏዊ አስተዳደር እና ለሀብት ምዝበራ የፈጠረውን ክፍተት ለመግታት ብሎም ለካህናት እና ለምእመናን የቆየ ምሬት እልባት ለመስጠት፣ የሕገ ቤተ ክርስቲያኑ አንቀጽ 50 ንኡስ አንቀጽ(1) ድንጋጌ እንዲሻሻል ወስኗል።

ቅዱስ ሲኖዶስ ባደረገው የድንጋጌ ማሻሻያ፣ ርእሰ መዲናዪቱ አዲስ አበባን የብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርኩ ልዩ ሀገረ ስብከት ያደረገው አንቀጽ፣ ወጥቶ፣ አዲስ አበባ ሀገረ ስብከት፣ እንደ ሌሎቹ አህጉረ ስብከት ራሱን ችሎ ሊቀ ጳጳስ ተመድቦለት የሚመራ ይኾናል፡፡ በዚህም መሠረት ምልዓተ ጉባኤው፣ ብፁዕ አቡነ መልከ ጼዴቅን ለሀገረ ስብከቱ ሊቀ ጳጳስ አድርጎ መድቧል።

የቤተ ክርስቲያናችን መንፈሳዊ እና አስተዳደራዊ ሕግ አውጪ እና ወሳኝ አካል የኾነው ቅዱስ ሲኖዶስ፣ በሕገ ቤተ ክርስቲያን የተደነገገን አንቀጽ፥ በከፊል ወይም በሙሉ የመለወጥ፣ የማሻሻል እና የመሰረዝ ሙሉ ሥልጣን ያለው በመኾኑ፣ የአህጉረ ስብከት ማዕከል የኾነው የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት፥ በስብከተ ወንጌል፣ በሰው ሀብት አስተዳደር፣ በፋይናንስ አያያዝ እና በንብረት አጠባበቅ ረገድ ውጤታማ ተቋማዊ ለውጥ በማድረግ ተጠያቂነትን እንዲያስፈንና በአርያኣነት እንዲታይ፣ አስፈላጊ እና ወቅታዊ ነው ብሎ ያመንበትን የአንቀጽ 50 ድንጋጌ አሻሽሏል።

የመንበረ ሐዋርያት ወራሽ፣ የቤተ ክርስቲያኒቱ የመጨረሻ ከፍተኛ ሥልጣን ባለቤት፣ በመዋቅሯ ኹሉ የበላይ አካል የኾነና ልዩ ልዩ ሕጎችን፣ ደንቦችንና መመሪያዎችን የማውጣት እና የመወሰን ሥልጣን ያለው ቅዱስ ሲኖዶስ ያሳለፋቸውን ውሳኔዎች፥ ኦርቶዶክሳውያን ካህናት፣ ምእመናንና ወጣቶች ኹሉ  የመቀበል፣ የመጠበቅ እና የማስጠበቅ ግዴታ አለብን፡፡ የቤተ ክርስቲያናችን ልዕልና ሊጠበቅ የሚችለው፣ በበላይነት የመምራት እና የማስጠበቅ ሓላፊነት ያለው ቅዱስ ሲኖዶስ የሚያሳልፈው ውሳኔ ሲከበር እንደኾነ አሌ የሚባል አይደለም።

ይኹን እንጂ፣ በላይኛው መዋቅር ዙሪያ የተኮለኮሉ እና መዋቅሩን የግል መጠቀሚያ በማድረግ ጥቅማቸውን ለማስቀጠል የቋመጡ፣ በተዋረድም በመዋቅር ውስጥ የተሸሸጉ፣ በአፍቅሮተ ነዋይ የሰከሩ እና ለተንደላቀቀ ሥጋዊ ኑሯቸው በኔትወርክ ተሳስረው እየደለሉ ጥቅማቸውን ከማሳደድ በቀር ሞያ የሌላቸው አማሳኞች፣ የቅዱስ ሲኖዶስን ወሳኔ ከመቀበል ይልቅ ተግባራዊነቱን በልዩ ልዩ የአድማ ቅስቀሳ ለማስተሃቀር መሰለፋቸው አያስገርምም። ለማይሞላው ቀፈታቸው እና ገደብ አልባ ፍትወታቸው ሲሉ ቤተ ክህነታችን ከብልሹ አሠራር እንዲላቀቅ አይሹም።

በባሕርይዋ ቅድስት የኾነችው ኦርቶዶክሳዊት ቤተ ክርስቲያን፣ በአስተዳደር ድክመት የተነሣ ዘመኑን ባለመዋጀቷ እየተነቀፈች መዘበቻ ብትኾን፣ ዕድሜ ዘመናቸውን በትምህርት ያሳለፉ ሊቃውንት፣ ሌት ተቀን በአገልግሎት የሚደክሙ ካህናት እና መምህራን የሚገባቸውን መብት እና ጥቅም ተነፍገው ቢንገላቱ፣ ቀናዒ ምእመናን በእነርሱ ነውር ተሸማቅቀው በዐደባባባይ ቢያፍሩ፣ ጥቂት የማይባሉትም ተሰነካክለው ወደ ሌላ ቢኮበልሉ በአጠቃላይ፣ ቤተ ክርስቲያን ከመሠረታዊው የስብከተ ወንጌል ተልእኮዋ እና ከማኅበራዊ ልማት አገልግሎትዋ ብትደናቀፍ አንዳችም አይገዳቸውም፡፡ በነባሩ የልዩ ሀገረ ስብከት ድንጋጌ፣ ቅዱስነታቸው ዕለታዊ እና ዝርዝር ጉዳዮችን በቅርበት ከመከታተል አኳያ የተፈጠረውን ክፍተት ተጠቅመው፣ ሕገ ወጥ ሀብትን ለግላቸው እያደለቡ መቀጠልን ይመርጣሉ፡፡

እነኚህ ግለሰቦች እና ቡድኖች፣ የቅዱስ ሲኖዶስ ርእሰ መንበር እና ርእሰ አበው የኾኑት ብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርካችን፣ ሕገ ቤተ ክርስቲያኑን ጠብቀው እና አስጠብቀው አጠቃላይ አመራር የመስጠት ሓላፊነት እንዳለባቸው በቅጡ አይረዱም፤ በአንድ ሀገረ ስብከት ሳይወሰኑ በኹሉም አህጉረ ስብከት፣ የቅዱስ ሲኖዶስን ውሳኔ እና መመሪያ ለማስፈጸም ቅዱስነታቸው በበላይነት የሚከታተሉ እና የሚቆጣጠሩ መኾኑን አያስተውሉም፡፡ እያወቁም ቢኾን፣ አዛኝ እና ተቆርቋሪ መስለው በመቅረብ፣ ቅዱስነታቸው ከሚታወቁበት መርሕ እና አባታዊ አቋም ጋራ የማይስማማ ባዕድ ዐሳብ በማንሣት ውዥንብር ሲፈጥሩ ታይተዋል። በቅዱስ ሲኖዶስ የስብሰባ ሥነ ሥርዓት በተለይ አስተዳደራዊ ጉዳዮችን በተመለከተ፣ በአባቶች መካከል የሚንጸባረቀውን ጤናማ የሐሳብ ልዩነት እና አቋም መነሻ አድርገው የራሳቸውን ቅርፅ በመስጠት፣ የማይደግፉትን ወገን ለማሳጣት የሔዱበት ርቀት፣ የገቡበትን ፅልመታዊ እንቅስቃሴ እና ድብቅ የጥፋት አዘቅት የሚያጋልጥ ነው።

የቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ፣ ሕገ ቤተ ክርስቲያኑን በማሻሻል አግባብ የልዩ ሀገረ ስብከት ድንጋጌ እንዲለወጥ ውሳኔ ካሳለፈበት ሥርወ ምክንያት እና አግባብ ውጪ ሌላ ትርጉም እየሰጡ፣ በቅንነት በጎ ሐሳብ ሲሰነዝሩ የነበሩ ብፁዓን አባቶችን ባልተገባ መንገድ እየፈረጁ ልዩነትንና ውዝግብን ለማስፋት ሞክረዋል። በዋናነትም ቅዱስነታቸው፣ ቅዱስ ሲኖዶስ ለሚያሳልፋቸው ውሳኔዎች ተገዢ የመኾናቸውን የማይናወጥ አቋም በተሳሳተ መንገድ በመረዳት፣ በማስረዳት እና ከፋፋይ ቅስቀሳ በማካሔድ፣ ከላይ እስከ ታች የዘረጉትን የጥቅም ትስስር ለማስቀጠል፣ ቤተ ክርስቲያንን አዳክሞ ለፀራውያን ጥቃት እና ለፖሊቲከኞች ጣልቃ ገብነት አሳልፎ ለመስጠት የደረሱበትን የድፍረት ጥግ በገሃድ ለመገንዘብ ችለናል።

በሌላው ጽንፍ ደግሞ፣ በዘመኑ የጎሠኝነት ደዌ የተመቱ፣ የቤተ ክርስቲያን አንድነት መጠበቅ ዕንቅልፍ የሚነሳቸው፣ እንደየዘመኑ የፖለቲካ ቅኝት አሰላለፋቸውን እየለዋወጡ ቤተ ክርስቲያኒቱን መቀፍደድ የሚፈልጉ፣ የመንፈስ ቅዱስን ይኹንታ በሥጋዊ መሻታቸው ለመተካት የሚያደቡ ወደረኞች፣ በልዩ ልዩ  ሚዲያዎች እና የኅትመት ውጤቶች ቅዱስነታቸውን በማጥላላት፣ ባልዋሉበት እና በማያውቁት ጉዳይ በሐሰት ለመክሠሥ የሚያደርጉት አፍራሽ እንቅስቃሴ፣ ሐዋርያዊት፣ ጥንታዊት እና ታሪካዊት የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያንን ልዕልና ለመዳፈር የቃጡበት ነው፡፡

በመኾኑም፣ በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን  የሰንበት ት/ቤቶች አንድነት፦

  •  በመዋቅር ውስጥም ኾነ በውጪ ኾናችኁ፣ ቅዱስነታቸውንና ሌሎችንም ብፁዓን አባቶችን አስመልክቶ ሐሰተኛ ንግግር የምታስተላልፉ፣ ጸያፍ እና ተገቢ ያልኾነ ጽሑፍ የምታሰራጩ፣ ገጸ ሥዕሎቻቸውንና ምስል ወድምፃቸውን በመጠቀም፣ ሐሰተኛ ዘገባ በመሥራት ስም በማጥፋት ተግባር  ላይ የተሰማራችኹ አንዳንድ አካላት ከድርጊታቸሁ እንድትቆጠቡ፤ ይልቁንም የሚያቀራርብ፣ አንድነትን የሚያጸና እና ሰላምን የሚያስፍን በጎ ፍሬ ያለው ተግባር ላይ እንድትሰማሩ አጥብቀን እናሳስባለን።
  • ቅዱስ ፓትርያርኩ በፈቃደ እግዚአብሔር ለታላቋ ቤተ ክርስቲያን የተሾሙ፣ እስከ ዓረፍተ ዘመናቸው በመንበሩ የሚቆዩ የኦርቶዶክሳውያን ኹሉ አባት ናቸው። በግለሰቦች ጩኸት፣ ስሜት እና ፍላጎት  ሥልጣነ ፕትርክናውንና ዘመነ ክህነታቸውን የሚሽር እና የሚለወጥ አንዳችም ነገር አይኖርም። ይህንም በማድረግ በዘመናችን ጥቁር ታሪክ እንዲመዘገብ ከቶ አንፈቅድም።

በመኾኑም፣ በማወቅም ኾነ ባለማወቅ፣ የቤተ ክርስቲያናችንን ሰላም ለማደፍረስ እኵይ ዓላማ አንግባችኹ የተሰለፋችኹ ከአጥቢያ እስከ ከፍተኛ ሓላፊነት ያላችኹ፣ በቅዱስ ፓትርያርኩ ስም የምትነግዱ፣ “ተገፉ፤ ጫና ተደረገባቸው” ባይ የጨለማው ቡድን አጋፋሪዎች፣ ያለፈው ዘመን ይበቃልና ከዚኽ ድርጊታችኹ ታቅባችኹ ንሥሓ እንድትገቡ እንመክራለን። በደመ ክርስቶስ የተመሠረተች፣ በመንፈስ ቅዱስ የጸናች ቤተ ክርስቲያናችን፣ በእንዲህ ዓይነቱ የእናንተ ክፋት አልቆመችም፤ በእናንተም አትፈርስም። ይልቁንም፣ ያለፈው ዘመን ይበቃል፤ ወደ ልባችኹ ተመለሱ፤ ከቤተ ክርስቲያኒቱ፣ ከቅዱስነታቸው እና ከብፁዓን አባቶች ላይ እጃችኹን ሰብስቡ።

ያለው እና ተከታዩ ትውልድ የሚረከባት ቤተ ክርስቲያን፥ የጥቅመኞች፣ የጎሠኞች፣ የሥልጣን ጥመኞች እና የልዩ ተልእኮ አራማጆች መፈንጫ ስትኾን በባይተዋርነት እንደማንመለከት አስረግጠን ለመናገር እንወዳለን። ከምእመናን ቤተሰቦቻችን ጋራ በመኾን፣ ቅዱስ ሲኖዶስ ለቤተ ክርስቲያን አጠቃላይ ተቋማዊ ለውጥ ያሳለፋቸው ጥናታዊ ውሳኔዎች ሳይሸራረፉ በአፋጣኝ ተግባራዊነታቸው እንዲጀመር፣ ከቤተ ክህነታችን አመራር እና ከአስተዳደር ጎን በመቆም፣ የበኩላችንን ሞያዊ እገዛ በማበርከት እና የምልዓተ ወጣቱን ድጋፍ በማስተባበር ቤተ ክርስቲያናችንን ከምዝበራ፣ ከማንኛውም ተጽዕኖ እና ጥቃት እንታደጋለን፤ ክብሯንና ልዕልናዋን ተረክበን እናስረክባለን።

በመጨረሻም፣ የቅዱስ ሲኖዶስ ጽ/ቤት እና የመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተ ክህነት ጽ/ቤት፣ የቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ ቀደም ሲል ባሳለፈው ውሳኔ መሠረት፣ የብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርክ ልዩ ጽ/ቤት፥ የመንበረ ፕትርክናውን ክብር፣ መልካም ስም እና ዝና በሚመጥን የፕሮቶኮል ሠራተኞች እና የልዩ ልዩ ዘርፍ አማካሪዎች ቡድን በማዋቀር እና በማደራጀት፣ እየተስተዋሉ የሚገኙ ችግሮች እና ክፍተቶች እንዳይደገሙ ይደረግ ዘንድ በአክብሮት እያስታወስን፣ ከቅዱስ ሲኖዶስ ውሳኔ ጎን በመቆም ለአፈጻጸሙ የሚቻለንን ጥረት እንደምናደርግ በልጅነት አንደበት ለማሳሰብ እንወዳለን።

ቸሩ እግዚአብሔር የአገራችንን ሰላም የቤተ ክርስቲያናችንን አንድነት ይጠብቅልን፡፡

የሰንበት ትምህርት ቤቶች አንድነት

ኅዳር 7 ቀን 2013 ዓ.ም.

ሊቀ አእላፍ ቀሲስ በላይ መኰንን የጠቅላይ ቤተ ክህነት ምክትል ሥራ አስኪያጅ ኾነው ተሾሙ

  • ቅዱስ ሲኖዶስ በወሰነው መሠረት በቅዱስ ፓትርያርኩ ተሹመው ተመድበዋል፤
  • የጠቅላይ ቤተ ክህነት ጽ/ቤት የ5 መምሪያዎች ዋና ሓላፊዎች ዝውውር ተደረገ፤
  • ንቡረ እድ ኤልያስ ኣብርሃ ወደ መሪ ዕቅድ ትግበራ ጽ/ቤት ተዛውረው ይሠራሉ፤

***

ሊቀ አእላፍ ቀሲስ በላይ መኰንን፣ የመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተ ክህነት ጽ/ቤት ምክትል ሥራ አስኪያጅ ኾነው እንዲሠሩ በብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርኩ ተሾሙ፡፡

ቋሚ ሲኖዶስ፣ ከትላንት በስቲያ ረቡዕ፣ ኅዳር 2 ቀን 2013 ዓ.ም. ባካሔደው ሳምንታዊ ስብሰባ ላይ፣ ሊቀ አእላፍ ቀሲስ በላይ፣ በጠቅላይ ጽ/ቤቱ ጠቅላይ ሥራ አስኪያጅ ብፁዕ አቡነ ያሬድ በዕጩነት ቀርበው ከተመረጡ በኋላ፣ በቅዱስ ፓትርያርኩ በተፈረመ ደብዳቤ በምክትል ሥራ አስኪያጅነት ተሹመዋል፡፡

የሊቀ አእላፍ ቀሲስ በላይ መኰንን ሹመት፣ የቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ፣ በጥቅምቱ የመጀመሪያ ዓመታዊ መደበኛ ስብሰባው፣ “የኦሮሚያ ቤተ ክህነት አደራጅ ነን” በማለታቸው ሥልጣነ ክህነታቸው ታግዶ ከነበሩት ጋራ በተደረገው ውይይት መግባባት ላይ በመደረሱ፣ ክህነታቸው የተያዘባቸው ካህናት ሥልጣነ ክህነታቸው ተለቆላቸው በቤተ ክርስቲያን መዋቅር ውስጥ የሥራ መደብ ተሰጥቷቸው እንዲያገለግሉ በወሰነው መሠረት የተፈጸመ መኾኑ ታውቋል፡፡  

በኦሮሚያ ክልል በሚገኙ አህጉረ ስብከት፣ በአስተዳደር ችግር እና በቋንቋ አገልግሎት ውስንነት ያጋጠመውን የሐዋርያዊ ተልእኮ አፈጻጸም መዳከም፣ በጠቅላይ ቤተ ክህነት ጽ/ቤት ሥር በሚቋቋም ጠንካራ አካል በኩል በአንድነት ለመፍታት ተስማምተው ወደ አሐቲ ቤተ ክርስቲያን መዋቅር የተመለሱት ሊቀ አእላፍ ቀሲስ በላይ መኰንን፣ ቀደም ሲል በዚኹ የሓላፊነት ደረጃ በመሥራታቸው ለሹመቱ እንግዳ አይደሉም፡፡

ብፁዕ አቡነ እስጢፋኖስ የጅማ እና የምዕራብ ጎንደር አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ፣ የጠቅላይ ጽ/ቤቱ ጠቅላይ ሥራ አስኪያጅ በነበሩበት ወቅት፣ ሊቀ አእላፍ ቀሲስ በላይ፣ ለአራት ዓመት ከኹለት ወራት ምክትል ዋና ሥራ አስኪያጅ በመኾን ሠርተዋል፡፡ ከዚያም ጋራ፥ የስብከተ ወንጌል እና ሐዋርያዊ ተልእኮ መምሪያ ዋና ሓላፊ፣ በቤቶች እና ሕንፃዎች አስተዳደር እና ልማት ድርጅት፣ በሰዋስወ ብርሃን ቅዱስ ጳውሎስ መንፈሳዊ ኮሌጅ ዋና ዲን፣ የሕግ አገልግሎት መምሪያ ዋና አማካሪ እንዲሁም የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት ዋና ሥራ አስኪያጅ ኾነው ሠርተዋል፡፡ በትምህርት ዝግጅታቸውም፣ በሕግ የመጀመሪያ ዲግሪ እና በንግድ አስተዳደር ኹለተኛ ዲግሪ አግኝተዋል፡፡

የቤተ ክርስቲያንን የሥራ አስፈጻሚነት እና የአስተዳደር ተግባራት በከፍተኛ ደረጃ ለማከናወን ሥልጣን ለተሰጠው የጠቅላይ ቤተ ክህነት ጽ/ቤት፣ በምክትል ሥራ አስኪያጅነት የሚሾም ሓላፊ፥ ሥልጣነ ክህነት ያለው ኾኖ፣ በነገረ እግዚአብሔር ወይም በአንድ የጉባኤ ትምህርት የተመረቀ፣ በቂ የቤተ ክርስቲያን ትምህርት ያለውና በአስተዳደር ችሎታው ብቁ መኾን እንዳለበት፣ በሕገ ቤተ ክርስቲያኑ አንቀጽ 44 ንኡስ አንቀጽ (4) ተደንግጓል፤ ለምርጫውም፣ ተወዳዳሪ ዕጩዎች መቅረብ እንዳለባቸው በድንጋጌው ተመላክቷል፤ የአገልግሎት ዘመኑም፣ የጠቅላይ ሥራ አስኪያጁ የሥራ ዘመን ማለትም ለሦስት ዓመታት እንደኾነ በድንጋጌው ሰፍሯል፡፡

በሌላ በኩል፣ የጠቅላይ ቤተ ክህነት ጽ/ቤት ምክትል ሥራ አስኪያጅ ኾነው የቆዩት ርእሰ ደብር መሐሪ ኃይሉ፣ ወደ ትንሣኤ ማሳተሚያ ድርጅት ተዛውረው በዋና ሥራ አስኪያጅነት እንዲሠሩ ተመድበዋል፡፡ የትንሣኤ ማሳተሚያ ድርጅት ዋና ሥራ አስኪያጅ ኾነው ሲሠሩ የቆዩት ንቡረ እድ ኤልያስ ኣብርሃ፣  ወደ መሪ ዕቅድ ትግበራ ጽ/ቤት ዋና ሓላፊነት ተዛውረው እንዲሠሩ ተመድበዋል፡፡

የመሪ ዕቅድ ጽ/ቤትን ለማደራጀት እና የትግበራ ፕሮጀክቱን ለማስጀመር፣ የቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ፣ የ2.5 ሚሊዮን ብር በጀት አጽድቋል፡፡ ብፁዕ ጠቅላይ ሥራ አስኪያጁ ለ39ኛው አጠቃላይ ሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤ ዓመታዊ ስብሰባ ባቀረቡት ሪፖርት፣ የጽ/ቤቱ መተዳደሪያ ደንብ በቋሚ ሲኖዶስ እንዲጸድቅ መደረጉንና ትግበራውን የሚመራ እና የሚያስተባብር ምክትል መምሪያ ሓላፊ እንዲመደብለት ተደርጎ ሥራውን ማከናወን መጀመሩን አስታውቀዋል፡፡

ትላንት በዋና ሓላፊነት ከተመደቡት ንቡረ እድ ኤልያስ ኣብርሃ ቀደም ሲል፣ የትግበራ ጽ/ቤቱ ምክትል ሓላፊ ኾነው የተመደቡት፣ የቀድሞው የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት ዋና ሥራ አስኪያጅ መ/ር ይቅር ባይ እንዳለ ናቸው፡፡ ቅዱስ ሲኖዶስ በጥቅምት ወር 2011 ዓ.ም. ባሳለፈው ውሳኔ መሠረት፣ የመሪ ዕቅድ ጽ/ቤቱ፣ የትግበራ ቲሞችን በማቋቋም፣ ከይዘት ክለሳው እስከ ክንውኑ ሥራውን የሚፈጽሙ ባለሞያዎችን በአግባቡ ቀጥሮ ማሠራት ይጠበቅበታል፡፡

በተጨማሪ የዝውውር ዜና፣ የስብከተ ወንጌል እና ሐዋርያዊ ተልእኮ መምሪያ ዋና ሓላፊ ኾነው ሲሠሩ የቆዩት መጋቤ ሰላም ቀሲስ ሰሎሞን ቶልቻ፣ ወደ ሰበካ ጉባኤ ማደራጃ መምሪያ ተዛውረው በዋና ሓላፊነት እንዲሠሩ ተመድበዋል፡፡ የማደራጃ መምሪያው ዋና ሓላፊ ኾነው ሲሠሩ የቆዩት መጋቤ ሐዲስ ሐዋዘ ብርሃን ጫኔ ደግሞ፣ ወደ ስብከተ ወንጌል እና ሐዋርያዊ ተልእኮ መምሪያ ተዛውረው በዋና ሓላፊነት እንዲሠሩ መመደባቸው ተገልጿል፡፡

የዋና ሓላፊዎቹ መዛወር ዓላማ፣ “ሥራንና ሠራተኛን ለማገናኘት ሲባል” እንደኾነ፣ በብፁዕ ጠቅላይ ሥራ አስኪያጁ ተፈርሞ በየስማቸው ከደረሳቸው ደብዳቤ ለመረዳት ተችሏል፡፡ በሕገ ቤተ ክርስቲያኑ አንቀጽ 42 ንኡስ አንቀጽ 6 መሠረት፣ የመምሪያዎች እና የድርጅቶች ሓላፊዎች የሥራ ዝውውር እና ዕድገት፣ በብፁዕ ጠቅላይ ሥራ አስኪያጁ አቅራቢነት ተጠንቶ ቅዱስ ፓትርያርኩ ሲስማማበት ተፈጻሚ እንዲኾን ይደረጋል፡፡

የብፁዕ አቡነ ኤጲፋንዮስ ሊቀ ጳጳስ ሥርዓተ ቀብር ተፈጸመ

የምዕራብ ሸዋ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ የነበሩት ብፁዕ አቡነ ኤጲፋንዮስ ሥርዐተ ቀብር ተፈጸመ፡፡

ብፁዕነታቸው፣ ሀገረ ስብከቱን በመምራት ላይ እያሉ ባደረባቸው ሕመም ከሓላፊነት ተገልለው እና በሕክምና ሲረዱ ቆይተው፣ ትላንት ኅዳር 2 ቀን 2013 ዓ.ም. በተወለዱ በ72 ዓመት ዕድሜያቸው ያረፉ ሲኾን፣ ዛሬ ጠዋት፣ በመንበረ ጸባኦት ቅድስት ሥላሴ ካቴድራል ሥርዓተ ቀብራቸው ተፈጽሟል፡፡

ብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርክ አቡነ ማትያስ፣ ብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት፣ የጠቅላይ ቤተ ክህነት ጽ/ቤት እና የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት ጽ/ቤት ሓላፊዎች፣ የገዳማት እና አድባራት አስተዳዳሪዎች እንዲሁም ምእመናንና ወዳጆቻቸው በተገኙበት በተፈጸመው ሥርዓተ ቀብር፣ የብፁዕነታቸው ዜና ሕይወት እና ሥራ፣ በብፁዕ አቡነ ዮሴፍ የቅዱስ ሲኖዶስ ዋና ጸሐፊ እና የሲዳማ እና ጌዲዮ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ በንባብ ተሰምቷል፡፡

ብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርኩም፣ “ብፁዕ አቡነ ኤጲፋንዮስ፣ መንፈሳዊ አገልግሎት አበርክተው በሕግ እና በሥርዓት ኖረው ወደ አምላካቸው ሔደዋል፤” በማለት የማጽናኛ ትምህርት እና ቡራኬ ሰጥተዋል፡፡

የብፁዕነታቸው በረከት ይድረሰን፤ አሜን፡፡

የዘገባ ምንጭ እና ፎቶዎች: ኢኦተቤ ቴቪ እና የኢኦተቤ ሕዝብ ግንኙነት መምሪያ

ብፁዕ አቡነ ኤጲፋንዮስ ዐረፉ

  • የቀብር ሥነ ሥርዐታቸው ነገ ጠዋት በ3፡00 በመንበረ ጸባኦት ቅድስት ሥላሴ ካቴድራል ይፈጸማል

የቀድሞው የምዕራብ ሸዋ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ የነበሩት፣ ብፁዕ አቡነ ኤጲፋንዮስ፣ ዛሬ ጠዋት ዐርፈዋል፡፡

ከሓላፊነታቸው ተገልለው በመንበረ ፓትርያርኩ በሚገኘው ማረፊያቸው ለረጅም ጊዜ በሥጋ ሕመም የቆዩት ብፁዕነታቸው፣ ዛሬ ረቡዕ፣ ኅዳር 2 ቀን 2013 ዓ.ም.  ጠዋት በሞተ ሥጋ ተለይተውናል፡፡

ብፁዕ አቡነ ኤጲፋንዮስ፣ በአምስተኛው ፓትርያርክ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ጳውሎስ አንብሮተ እድ፣ ሐምሌ 5 ቀን 1991 ዓ.ም. ኤጲስ ቆጶስነት ከተሾሙት 16 ብፁዓን አባቶች አንዱ ነበሩ፡፡

በፊት ስማቸው አባ አምኃ ሥላሴ አሳየኸኝ ይባሉ የነበሩ ሲኾን፣ ብፁዕ አባ ኤጲፋንዮስ ተብለው ለከፋ ሸካ ሀገረ ስብከት ተመድበው ነበር ሐዋርያዊ አገልግሎታቸውን የጀመሩት፡፡

የብፁዕ አቡነ ኤጲፋንዮስ የቀብር ሥነ ሥርዐት፣ ነገ ኀሙስ፣ ኅዳር 3 ቀን 2013 ዓ.ም. ከጠዋቱ በ3፡00፣ ሊቀ ሥልጣናት ኾነው በአስተዳዳሪነት በመሩት በመንበረ  ጸባኦት ቅድስት ሥላሴ ካቴድራል፣ ብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርክ አቡነ ማትያስ፣ ብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት፣ የጠቅላይ ቤተ ክህነት የመምሪያ ሓላፊዎች እና የድርጅቶቹ ሓላፊዎች፣ የአዲስ አበባ አድባራት እና ገዳማት ሓላፊዎች፣ ወዳጅ ዘመዶቻቸው በተገኙበት እንደሚፈጸም፣ የጠቅላይ ቤተ ክህነት ሕዝብ ግንኙነት መምሪያ በፌስቡክ ገጹ አስታውቋል፡፡